ቋሚ ኮሚቴዎች ባደረጉት ድጋፍና ክትትል በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ማረም ተችሏል- የሀዲያ ዞን ምክር ቤት

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 06/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሀዲያ ዞን ምክር ቤት 4ኛ ዙር 12ኛ ዓመት 23ኛ የስራ ዘመን መደበኛ ጉበኤውን እያካሄደ ይገኛል፡፡

ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ እቴነሽ ሙሉጌታ ምክር ቤቱ ከመደበኛ ስራ ጎን ለጎን በቋሚ ኮሚቴ አማካይነት የአስፈጻሚ ተቋማትን የስራ አፈጻጸም በዓመት አራት ጊዜ ክትትልና ድጋፍ ማድረጉን አንስተዋል።

ቋሚ ኮሚቴዎቹ ባደረጉት ድጋፍና ክትትል የሕብረተሰቡ የመልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች መመለሳቸውን የተናገሩት ዋና አፈ ጉባኤዋ የኦዲት ግኝቶችን መሠረት በማድረግ ተጠያቂነት እንዲሰፍን ምክር ቤቱ የድርሻውን እንደተወጣም አንስተዋል።

ምክር ቤቱ በተያዘው በጀት ዓመት ተግባሩን የበለጠ አጠናክሮ እንደሚያስቀጥል የተናገሩት ወ/ሮ እቴነሽ የምክር ቤቱ አባላትም ሆኑ ህብረተሰቡ ሚናውን እንዲጫወት ጠይቀዋል።

በዞኑ ዋና አስተዳደሪ በአቶ ማቴዎስ አኒዮ አቅረቢነት ወ/ሮ አለምነሽ ክፍሌ በምክር ቤቱ ለምክትል አፈ ጉባኤነት የቀረቡ ሲሆን ምክር ቤቱ ሹመቱን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።

ምክር ቤቱ በዛሬ ውሎው በዞኑ የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸም ሪፖርት ዙሪያ በስፋት ተወያይቷል፡፡ በነገው ዕለት የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የ2016 አፈጻጸም ሪፖርትና በ2017 ዕቅድ ዙሪያ ይመክራል፡፡

በተጨማሪም በ2017 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ላይ ተወያይት የሚያጸድቅ ሲሆን የተለያዩ ሹመቶችንም እንደሚጸድቅ ይጠበቃል።

ዘጋቢ፡ ጌታቸው መጮሮ -ከሆሳዕና ጣቢያችን