በደቡብ ኦሞና ኣሪ ዞኖች መካከል የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ተካሄደ

በደቡብ ኦሞና ኣሪ ዞኖች መካከል የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በደቡብ ኦሞና ኣሪ ዞኖች መካከል የወንድማማችነትና የአንድነት የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለአቅመ ደካማ ማህበረሰብ ክፍሎችና ለተማሪዎች ድጋፍ የመስጠት መርሐ ግብር ተካሂዷል።

በጎነት ለአብሮነት በሚል መሪ ቃል የደቡብ ኦሞ ዞን ወጣቶች በኣሪ ዞን ደቡብ ኣሪ ወረዳ በጋዜር ሆስፒታል ለሚገኙ ነፍሰጡር እናቶችና ለተመረጡ አቅመ ደካማ ቤተሰብ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ አድርገዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት በወጣቶች ሊግ አስተባባሪነት የተዘጋጀው መርሐ ግብር በሁለቱ ዞኖች አንድነታቸውንና አብሮነታቸውን የሚያጠናክር የችግኝ ተክለና የበጎ ተግባር ሥራ አካሂደዋል።

በክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በክልሉ በ12 ዞኖች እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የወጣቶች ሊግ ኃላፊ አቶ ሚካኤል ዋዶ ወጣቱ ትውልድ ከአባቶቹ የወረሰውን አብሮነትና ወንድማማችነት በመጠናከር ወጣቶች በጉልበታቸውና በዕውቀታቸው ማህበረሰቡን እንዲያገለግሉ ጥሪ አቅርበዋል።

የኣሪ ዞን ዋና አሰተዳደር አቶ አብርሃም አታ በመርሐ ግብሩ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት በተባባረ አንድነት በመነሳት ወጣቶች ለበጎ ተግባር እየሰጡ ያሉት ቦታ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው የደቡብ ኦሞ ዞን በጎ ፈቀደኛ ወጣቶች በኣሪ ዞን ላደረጉት ድጋፍም አመስግነዋል ።

የደቡብ ኦሞ ዞን ሳምራዊ በጎ አድራጎት ማህበር ምክትል ሰብሳቢ ወጣት ደጉ አሸናፊ ከዞኑ ህዝብ ለበጎ አላማ ባሰባሰቡት ገንዘብ ለተማሪዎች ቁሳቁስና ለነፍሰጡር እናቶች የፉርኖ ዱቄት ዘይትና ሌሎችም ድጋፎች ማድረጋቸውን አስረድተዋል።

በሁለቱ ዞኖች መካከል ወንድማማችነትንና አብሮነትን በማጠናከር በጋራ እንሰራለን ያሉት በጎ ፈቀደኛ ወጣቶች በበጎ አገልግሎት የተከናወኑ መልካም ሥራዎች በሌላም ዘርፍ እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ መላኩ አድማሱ – ከጂንካ ጣቢያችን