ኃይል ቆጣቢ፣ ዘመናዊና ንጹህ የሆኑ የማብሰያ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽነት ለማስፋፋት እየሠራ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ
ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ በሚያካሂደው በዚሁ ፕሮግራም ዙሪያ ከክልል ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊዎችና ከዘርፉ ባለድርሻዎች ጋር ምክክር እያካሄደ ነው።
በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ዘርፍ ከፍተኛ አማካሪ አቶ ጎሳዬ መንግሥቱ እንደገለጹት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የንጹህ ማብሰያ ሀይል ተደራሽነትን ለማስፋፋት ታሳቢ ያደረገ ፕሮጀክት ቀርጾ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡
አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ለምግብ ማብሰያ የሚጠቀመው እንጨትና ከሰል ነው ያሉት ከፍተኛ አማካሪው በዚህም ከ150 ሺህ ሄክታር በላይ ደን ለውድመት ይዳረጋል ብለዋል።
እንደፈረንጆቹ የዘመን ቀመር በ2030 ኃይል ቆጣቢ፣ ዘመናዊና ንጹህ የማብሰያ ቴክኖሎጅዎችን ተደራሽነት በማስፋፋት በዘርፉ ይከሰቱ የነበሩ የጤና እና የአካባቢ ብክለት ችግሮችን ለመቅረፍ ግብ ተይዞ እየተሠራ እንደሚገኝም አቶ ጎሳዬ አመላክተዋል።
አሁናዊ የኢትዮጵያ የንጹህ ማብሰያ ቴክኖሎጂዎች ያሉበትን ደረጀ የሚያመለክት ገለፃም ተደርጓል።
ፕሮጀክቱን በተመለከተም የከልል ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ውይይት ያደርጉበታል።
ዘጋቢ፡ ጌታሁን አንጭሶ

More Stories
የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት 32ኛ የምክር ቤቶች የጋራ ምክክር ፎረም አካሄደ
ዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ደቡብ ሱዳንን አስጠነቀቀ
የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት 32ኛ የምክር ቤቶች የጋራ ምክክር ፎረም እያካሄደ ነው