የታክስ ህግ ተገዥነትን ዜጎች ላይ በማስፈን በገቢ አሰባሰብ ላይ እየተስተዋለ ያለውን ሕገ-ወጥነትን ለመከላከል እየተሰራ መሆኑን በፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር የጅማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አስታወቀ

የታክስ ህግ ተገዥነትን ዜጎች ላይ በማስፈን በገቢ አሰባሰብ ላይ እየተስተዋለ ያለውን ሕገ-ወጥነትን ለመከላከል እየተሰራ መሆኑን በፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር የጅማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አስታወቀ

በፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር፣ ጉምሩክ ኮሚሽንና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መንግስት ገቢዎች ቢሮ በቅንጅት የታክስና ጉምሩክ ክበብ ተማሪዎች ክልላዊ የጥያቄና መልስ ውድድር በሚዛን አማን ከተማ አካሂደዋል።

በውድድሩ ማጠቃለያ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ የታክስ ተገዥነት ሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ አትርሳው ሳህሌ እንደገለጹት የታክስ አዋጆችን ለመተግበር እንዲያስችልና የታክስ ህግ ተገዥነትን በዜጎች ላይ ለማስፈን እንደ ሀገር እየተሰራ ያለውን በጅማ ቅርንጫፍ ስር የሚገኙትን ግብር ከፋይና የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ግንዛቤ ለማሳደግ በሰፊው እየተሰራ ነው።

ልመናን፣ ብድርን፣ ግብር መሰወርን እንዲሁም ደረሰኝ አለመቁረጥን ለማስቀረትና ዜጎች ግብር የሚሰበሰበው ለሀገር ልማት ነው በማለት እንዲነሳሱ ለማስቻል በትምህርት ቤቶች የታክስና ጉምሩክ ክበባትን በማቋቋም፣ ከመሥራት ባለፈ ሞጁላር ስልጠና ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ በ3 ክፍል ለግብር ከፋዮች እየተሰጠ እንደሚገኝም አቶ አትርሳው አንስተዋል።

ይህንን ተከትሎም በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ከሚገኙት በተመረጡት 6 ትምህርት ቤቶች እየተተገበረ እንደሆነም ገልጸዋል።

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ገቢዎች ቢሮ ሀላፊ ወ/ሮ ሕይወት አስግድ በውድድሩ ማጠቃለያ ላይ ባደረጉት ንግግር ተወዳዳሪ ተማሪዎቹ ወደየመጡበት አካባቢ ተመልሰው ሲሄዱ የታክስ አምባሳደር በመሆን የታክስ ህግን በማስተማርና በመተግበር የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ ለማድረግ እንደሆነ አስገንዝበዋል።

በ2022 ዓ.ም ሀገራችን ኢትዮጵያ የራሷን ወጪ በራሷ ገቢ ለመሸፈን ግብ አስቀምጣ እየሰራች ያለችውን ለማሳለጥ ጠንካራ የታክስ ህግ ተገዥነትን ማስረጽ ተገቢ ስለሆነ ተማሪዎችም ይህንን ተገንዝበው ለሀገር ብልጽግና እንዲሰሩ መልዕክት አስተላልፈዋል።

በዚህ ዕለት የተገኙትም የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ አካሉ አለማየሁ የታክስና የጉሙሩክ ክበባትን በትምህርት ቤቶች በማቋቋም መምህራንና ተማሪዎች በታክስ ህግ ተገዥነት ላይ እንዲሰሩ ማድረግ ተማሪውና መምህሩ የሕብረተሰብ ሙሉ አካል እንደመሆናቸው በሕብረተሰቡ መካከል ያለውን የአመለካከት ችግር ለመቅረፍ ትልቅ አስተዋጽኦ ስላለው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

በቀጣይ በጅማ ከተማ ለሚካሄደው የታክስና ጉሙሩክ ክበብ ተማሪዎች ጥያቄና መልስ ውድድር ክልሉን ወክሎ የሚሳተፍ አንድ ተማሪ የተለየ ሲሆን ከስድስቱ ዞኖች ከመጡት ተማሪዎች ከአንደኛ ደረጃ እስከ ሶስተኛ ለወጡት ተወዳዳሪዎች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

ተወዳዳሪ ተማሪዎችም ውድድሩ በታክስ ህግ ተገዥነት ላይ ያላቸውን ዕውቀት የጨመረ መሆኑን ጠቁመው ወደ መጡበት ትምህርት ቤት ሲመለሱ ክበባትን በማጠናከርና በመሥራት የበኩላቸውን እንደሚወጡ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

ዘጋቢ፡ ወሰኑ ወዳጆ – ከሚዛን ጣቢያችን