ያለውን የምርጥ ዘር አቅርቦት እጥረት ለመቅረፍ ከግል ባለሀብቱ ጋር በመቀናጀት እየሰራ መሆኑን የምዕራብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ
ሀዋሳ፡ ሚያዝያ 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ያለውን የምርጥ ዘር አቅርቦት እጥረት ለመቅረፍ ከግል ባለሀብቱ ጋር በመቀናጀት እየሰራ መሆኑን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የምዕራብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ አስታውቋል።
በዞኑ በበልግ እርሻው 6 መቶ ሄክታር መሬት ምርጥ ዘር ለማምረት በዘር መሸፈኑም ተጠቁሟል።
የምዕራብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ መልኬ ኬላጌ እንደተናገሩት፤ በዞኑ ከአርሶ አደሩ የሚነሱ የምርጥ ዘር እጥረት መኖሩን ተናግረው ይህንን ችግር ለመፍታት በዞኑ ባሉ ባለሀብቶች 6 መቶ ሄክታር ምርጥ ዘር የማባዛት ስራ እየተሰራ ነው፡፡
አክለውም ኃላፊው ይህን ምርጥ ዘር የማባዛት ስራ ተጠናክሮ በማስቀጠል የዞኑን ብቻ ሳይሆን የክልሉን የምርጥ ዘር አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
የምዕራብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ኬኒ በበኩላቸው በዞኑ በኢንቨስትመንት የተሰማሩ በርካታ ባለሀብቶች ወደስራ መግባታቸውን ጠቁመው ምርጥ ዘር የሚያባዙ ባለሀብቶች ቢኖሩም ሌላ አከባቢ ምርጥ ዘሩ የሚቀነባበር መሆኑ ችግር እንደነበር ድርጅቱ በዚሁ አከባቢ ማቀናበሪያ የሚከፍት ከሆነ ዞኑ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አመላክተዋል። የተጠየቀውን ተጨማሪ የማስፋፊያ መሬትም ለመስጠት ለክልሉ ማሳወቃቸውንም ጠቁመዋል።
የመኢኒት ጎልዲያ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ ጎንጢዬ ፋጅዎ በበኩላቸው ድርጅቱ የተሰጣቸው መሬት በዘር መሸፈናቸውን ጠቁመው አርሶ አደሩ የሚጠይቀው የምርጥ ዘር እጥረት ለመፍታት ድርጅቱ እየሰራ ያለውን ስራ በማገዝ የአርሶ አደሩን የምርጥ ዘር እጥረት እንደሚቀርፉም ገልጸዋል።
በዞኑ በኢንቨስትመንት ከተሰማሩት ውስጥ መካከል ላይንስ ኢንተርናሽናል በምርጥ ዘር ብዜት የሚታወቅ ድርጅት ሲሆን ቀደም ሲል በኦሮሚያ ክልል ኖኖ ድርጅት አከባቢ ምርጥ ዘሮችን በማባዛት ለአርሶ አደሩ በማከፋፈል ሲሰራ መቆየቱን ነው የድርጅቱ ጎልዲያ ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅ አቶ ቢኒያም ዘነበ የተናገሩት።
በምዕራብ ኦሞ ዞኑም ይህንን ተግባር ለማስፋት በወሰዱት 5 መቶ ሄክታር ማሳ ወደተግባር መግባታቸውን ገልጸው እስካሁን 104 ሄክታር ማሳ ምርጥ ዘር መዝራታቸውን ጠቁመዋል።
በቀጣይም ድርጅቱ የራሱንም ማበጠሪያ ማሽን በመክፈትም የክልሉን የዞኑን የምርጥ ዘር አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
ደርጅቱ አሁን የተሰጠው መሬት ሙሉ በሙሉ በማልማቱ ተጨማሪ መሬት የጠየቁ ሲሆን የመንገድ ችግሩ ለስራቸውም አዳጋች እንደሆነባቸውም ተናግረዋል።
ዘጋቢ: አብዮት በቀለ – ከሚዛን ጣቢያችን

More Stories
በዶሮ እርባታ ዘርፍ በመሰማራት የተሻለ ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን የየም ዞን ሣጃ ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ ሰዎች ተናገሩ
የከተማውን መሰረተ ልማት ከማሟላት ባሻገር ለነዋሪዎች ምቹ እና ማራኪ በማድረግ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ
የዱራሜ ከተማ የኮሪደር ልማት ሥራ በአዲስ መልክ በዘመናዊ ዲዛይን እየተሰራ መሆኑን የዱራሜ ከተማ አስተዳደር ገለፀ