የአርባምንጭ ከተማን ፅዱና ውብ ለማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ከመቼውም ጊዜ በላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገለጸ

የአርባምንጭ ከተማን ፅዱና ውብ ለማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ከመቼውም ጊዜ በላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገለጸ

ሀዋሳ፡ የካቲት 21/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአርባምንጭ ከተማን ፅዱና ውብ ለማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ከመቼውም ጊዜ በላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጿል።

የከተማው ህዝብ ምክር ቤት 2ተኛ ዙር መርሀ ግብር 30ኛ መደበኛ ጉባኤውን የከተማ አስተዳደሩን የ6ወር እና የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እቅድ አፈጻጸም ገምግሞ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት እንዲጠናቁ ማድረግና የገቢ አቅምን ማሳደግ ዙሪያ ጉባኤው በስፋት ተወያይቷል።

የአርባምንጭ ከተማ ህዝብ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ጥሩነሽ ተስፋዬ በጉባኤው መክፈቻ ንግግራቸው አንደ ገለጹት በ2017 ዓ.ም የሚካሄደውን የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች  ክብረ-በአል ለማዘጋጀት የአርባምንጭ ከተማ በታጨች ማግስት ጉባኤው መካሄዱ ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።

የአርባምንጭ ከተማ ህዝብ ምክር ቤት አባላት የከተማ አስተዳደሩን የ6ወር እቅድ አፈጻጸም ገምግመዋል።

 የከተማዋን የገቢ አቅም ለማሳደግ ገቢ  ሰብሳቢ ተቋሙ የተጣለበትን ኃላፊነት በሚመጥን ሁኔታ ሊደራጅ ይገባል፤ የተጀመሩ ትላልቅ ፕርጀክቶች እንዲጠናቀቁ  ድጋፍ እንዲጠናከር እና ቆሞ ቀር ህንፃዎች ወደስራ እንዲገቡ በጉባኤው ከተነሱ ጥያቄዎች የሚጠቀሱ ናቸው።

የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃቤታዊ አገልግሎት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አጥናፉ ዲዶ በተሰነዘሩት ጥያቄዎች ዙሪያ ምላሽ ተሰጥተዋል።

የከተማዋን የገቢ አቅም ለማሳደግ የገቢ  ሰብሳቢ ተቋም ባለ አቅሙ የተጣለበትን በኃላፊነት  ለመወጣት ስራ ላይ መሆኑን ያስረዱት የከተማው ገቢዎች ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደግፌ አማረ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ ህዝባዊ መሰረት አለመያዝ፣ የባለሙያ ስነ-ምግባር መጓደል እና ሌሎች ችግሮች የገቢ አፈጻጸሙን ጎድተውታል።

የአርባምንጭ  ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ገዛኸኝ ጋሞ በከተማው እየጨመረ የመጣውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ የገቢ አቅምን ማሳደግ  የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል።

በከተማው አቅም ሊሰሩ የሚገቡ የልማት ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ እንደሚፈታ የጠቆሙት ከንቲባው በኦዲት ግኝት የተደረሰባቸውን ከ30 ሚሊየን የሚልቅን ውዝፍ እዳ ከህግ ጋር በማገናኘት ለማስመለስ እንደሚሰራ አብራርተዋል።

ጉባኤው የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የ6ወር አፈፃፀም ሪፓርት በማድመጥ የተለያዩ ጥያቄዎችን በማንሳት ምላሽ ከተሰጠ በኋላ ተጠናቋል። 

ዘጋቢ፡ አሰግድ ተረፈ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን