ህብረተሰቡ ያለሠላም ልማት እንደማይኖር ተገንዝቦ ለሠላም ቅድሚያ መሰጠት እንዳለበት ተጠቆመ

ህብረተሰቡ ያለሠላም ልማት እንደማይኖር ተገንዝቦ ለሠላም ቅድሚያ መሰጠት እንዳለበት ተጠቆመ

ሀዋሳ፡ የካቲት 20/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በምዕራብ ኦሞ ዞን የሱሪ ወረዳ ተመራጭ ወይዘሪት ትደነቅ ጉልዱ ህብረተሰቡ ያለሠላም ልማት እንደማይኖር ተገንዝቦ ለሠላም ቅድሚያ መሰጠት እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡

የክልሉ የፀጥታ አካላት፣ የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ ከየቀበሌዎች የተወጣጡ የጎሳ መሪዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች እንዲሁም የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በውይይቱ ተሳትፈዋል፡፡

ወይዘሪት ትደነቅ ጉልዱ እንደተናገሩት ሰላም የሁሉም ነገሮች መሰረት መሆኑንና ህብረተሰቡ ሠላም ከሌለ ልማት እንደማይኖር በአግባቡ ተገንዝቦ ለሠላም ቅድሚያ በመስጠት እና ችግሮችን በጋራ መፍታት ይጠበቅበታል ብለዋል።

አያይዘውም የስብሰባው ተሳታፊዎች በየደረጃው ለቤተሰቦቻቸውና ለጎረቤቶቻቸው ሰለ ሠላም መስበክ አለባቸው ነው ያሉት።

የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ኬኒ በወረዳ ባሉ ፀጥታ ችግሮች ልጆች በአግባቡ እንዳይማሩ፤ የጤናና የግብርና ባለሙያዎች በየቀበሌው ይሰጡት የነበረውን አግልግሎት በአግባቡ እየሰጠ ባለመሆኑ የሰላም ባለቤት የሆነው ሕዝብ ሚናውን በአግባቡ መወጣት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

አክለውም ለወረዳው የፀጥታ ችግሮች የሀገር ሽማግሌዎች፣ የጎሳ መሪዎችና የሀገር ባለ አባቶች ሚናቸው ከፍተኛ በመሆኑ ወረዳው ወደ ተረጋጋ ሠላምን እና ልማት እንዲገባ መስራት ይጠበቅባቸዋል ብልዋል።

እንደ አቶ ጌታቸው ገለፃ እናቶችና አባቶች ልጆቻቸው ወደ ጥፋት እንዳይገቡ መምከርና መቆጣት እንዳለባቸው እንዲሁም ህብረተሰቡ ልማት እንዳይሰራ የሚያደናቅፉ ወንጀለኞችን ተባብሮ ለህግ ማቅረብ እንዳለበት አስገንዝበዋል።

የሱሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ባሪ ቱሬ በበኩላቸው በጥቂት ግለሰቦች ህብረተሰቡ ማግኘት የነበረበትን የጤና፣ የትምህርትና የግብርና ዘርፍ አገልግሎቶች እያገኘ ባለመሆኑ የጎሳ መሪዎች የሠላም ሥራ በመስራት ባለሙያዎች በአግባቡ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ አለባቸው ብለዋል።

ምንጭ ፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት