የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነትን ከመጨመር ባለፈ የአካባቢውን ስነ-ምህዳር በማስተካከል ረገድ ድርሻ እንዳለው ተጠቆመ
ሀዋሳ፡ የካቲት 15/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነትን ከመጨመር ባለፈ የከርሰ-ምድርና ገጸ-ምድር ውሃ እንዲጨምር በማድረግና የአከባቢን ስነ-ምህዳር በማስተካከል የጎላ ድርሻ እንደለው ተገለፀ፡፡
በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ የሚገኘው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በኮንታ ዞን ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
አርሶ አደር ዓለሙ ኦታሞ፣ ታደለች ገብሬ እና ሌሎችም በወረዳው የሼታ ጫሬ ቀበሌ ነዋሪዎች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ሲያከናውኑ አግኝተናቸዋል።
አካባቢያቸው ተዳፋታማ እና በየጊዜው ለም አፈራቸውን ዝናብ አጥቦ በመውሰዱ ምክንያት ለረዥም ጊዜ ምርት ሳይሰጥ መቆየቱን ተናግረዋል።
አሁን ላይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተሰራው ስራ የአፈር ለምነቱ ጨምሮ ጥሩ ምርት እያገኙ መሆናቸውን ገልፀዋል።
በወረዳው የሼታ ጫሬ ቀበሌ ግብርና ባለሙያ አቶ ጋሻሁን ገብሬ በ2016 ዓመት በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ 2 ንዑስ ተፋሰሶች ተለይተው ለማልማት ወደ ስራ መገባቱን አስረድተዋል።
የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነትን ከመጨመር ባለፈ የከርሰ-ምድርና ገጸ-ምድር ውሃ እንዲጨምር የሚያደርግ መሆኑን የአመያ ዙሪያ ወረዳ ግብርና አከባቢ ጥበቃና ህብረት ሥራ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ካሣሁን ዳዕሞ አብራርተዋል።
በዚህም በወረዳው በዘንድሮ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ከ 7 ሺህ 2 መቶ በላይ ሄክታር መሬት ላይ 32 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ ታቅዶ ወደ ስራ በተገባው መሠረት በወረዳው በአማካይ 95 በመቶ ህብረተሰብ እየተሳተፈ እንደሚገኝ ኃላፊው ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ ደረጀ ተፈራ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኮረሪማ ምርት እየለማ መሆኑ ተገለጸ
በጎፋ ዞን ከ12 ሺህ በላይ ተማሪዎች ክልላዊ የ6ኛ ክፍል ፈተና እየተሰጠ ነው
የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች በመመለስ በኩል ከመንግስት ጥረት ባለፈ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሚና የጎላ መሆኑን የደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተመስገን ከበደ ተናገሩ