በወልቂጤ ከተማ ህዝባዊ  የውይይት እየተካሄደ ነው

ሀዋሳ፡ የካቲት 07/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) “ኅብረ ብሔራዊ ወንድማማችነት ለዘላቂ ሠላም እና ሁለንተናዊ ብልፅግና” በሚል መሪ ቃል ህዝባዊ የውይይት መድረክ በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።

በውይይት መድረኩ የተገኙት የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ እንደተናገሩት፤ መድረኩ በሀገሪቱ በ20 ከተሞች እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው በመድረኩ የሚነሳውን የህዝቡን ሀሳብ ወስደን የቀጣይ እቅድ አካል በማድረግ እንሠራለን ነው ያሉት።

በውይይት መድረኩ ላይ የሀገሪቱና የአካባቢው አጠቃላይ የሰላም፣ የልማት እና መልካም አስተዳደር እንዲሁም የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ጉዳይ ጭምር ያለበት ሁኔታ ምን እንደሚመስል  ውይይት የሚደረግ ስለመሆኑም አንስተዋል።

“ሀብትን የመፍጠር ጉዟችን ያጋጠሙ ተግዳሮቶችን እና የቀጣይ አቅጣጫዎች ሁሉን አቀፍ የህዝብ ተሳትፎ ለብልፅግና ጉዟችን ስኬታማነት” በሚል ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ እየቀረበ ይገኛል፡፡

በውይይት መርሃ-ግብሩ ላይ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፣ የብልጽግና ፓርቲ  ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና የሲዳማ ክልል ዋና የመንግስት ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ይግለጡ አብዛ እና የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማን ጨምሮ የዞንና የከተማው አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች እንዲሁም ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል።

ዘጋቢ፡ መሀመድ ሽሁር – ከወልቂጤ ጣቢያችን