ሀዋሳ፡ የካቲት 04/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኮሬ ዞን የኬሌ ከተማ አስተዳደር የ2016 የተፋሰስ ልማት ሥራን በይፋ አሰጀምሯል፡፡
ነዋሪዎች የከተማዋን ሕልውና እና ያለውን ሀብት ንብረታቸውን ለመጠበቅ ሲሉ ተራራውን ማልማት እንዳለባቸው በኮሬ ዞን የኬሌ ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።
የኮሬ ዞን መዲና ኬሌ ከተማ በሠንሰለታማ ተራሮች የተከበበች ስትሆን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተራሮቿ እየተራቆቱ እንደሆነ ነዋሪዎቿ ይናገራሉ።
የ2016 ተፋሰስ ልማት ሥራን ያስጀመሩት የኬሌ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዮሐንስ ኃይሉ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የምግብ ዋስትናን ከማስጠበቅ ባሻገር ለከተማዋ የሕልውና ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል።
ነዋሪዎች የከተማዋን ህልውና ለማስጠበቅ እና ሀብት ንብረታቸውን ከጎርፍ እና ናዳ ለመጠበቅ ሲሉ የተፋሰስ ልማትን በትኩረት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል።
በ2015 በተሰራው የተፋሰስ ልማት በከፊል ለውጥ እየታየ እንደመጣና ከተንከባከቡ ሰፊ ለውጥ ማየት እንደሚቻልም አመላክተዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ሰመረ አባተ በበኩላቸው፣ የዘንድሮ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በወጣቶች፣ በከተማ ማህበረሰብ እና በመንግስት ሰራተኞች አደረጃጀት እየተሠራ ነው ብለው፣ ከዚህ በፊት የለሙት ውጤት እንዲያሳዩ ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
በተፋሰስ ልማት ሥራ ላይ ተሳታፊዎች መካከል አቶ በዛብህ ቦጋለ፣ ጀንበሩ ጀጎ እና ባይዛር ባንድራ በሰጡት አስተያየት ሀገር የሚታድገው በጋራ የተፈጥሮ ሀብታችንን ስንጠብቅ ነው ብለዋል።
ያሉንን ረጅም እና ሰንሰለታማ ተራራን ማልማት ለቱሪዝም ዘርፍ ምቹ መደላደልን ይፈጥራል ያሉት ተሳታፊዎቹ፣ ከብቶችን በውስጡ ባለመልቀቅ እና ደኖችን ባለመቁረጥ መንከባከብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
በወሊድ ምክንያት የሚሞቱ እናቶችን ቁጥር ለመቀነስ የተጀመሩ ስራዎች አበረታች ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ገለጸ
የፃማኮ ብሄረሰብ የዘመን መለወጫ የ”ባርባይሳ” በዓል የህብረ ብሄራዊ አንድነት መገለጫ፣ የሰላምና የመተሳሰብ ምልክትነቱን በማግዘፍ ለዓለም አደባባይ ማብቃት ይገባል ሲሉ የክልሉ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ገለጹ
በ6 ወራት ውስጥ ሊመዘበር የነበረ ከ156 ሚሊየን 560ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉ ተገለጸ