በፋይናንስ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ እየገጠሙ ባሉ ችግሮች ላይ ትክክለኛ መረጃ አግኝተው ግልጸኝነትን መፍጠራቸውን የጌዴኦ ዞን ማዕከል የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ

በፋይናንስ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ እየገጠሙ ባሉ ችግሮች ላይ ትክክለኛ መረጃ አግኝተው ግልጸኝነትን መፍጠራቸውን የጌዴኦ ዞን ማዕከል የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ

በጥሬ ገንዘብ እጥረት እየገጠሙ ያሉ ችግሮችን በመፍታት አገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል ገቢን አሟጦ መሰብሰብ እንደሚያስፈልግ የዞኑ ፋይናንስ መምሪያ አሳስቧል።

የጌዴኦ ዞን አሰተዳደር የልማት ዕቅድ ባለሙያ አቶ ዳንኤል ሰዩም እና የዞኑ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰዉ ሀብት ልማት መምሪያ የሰው ሀብት ልማት አስተባባሪ ወ/ሮ ሳራ ሽብሩ አሁናዊ ተጨባጭ ሁኔታን ባለመገንዘብ ፋይናንስ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ሲነሱ በነበሩ ጉዳዮችና ቅሬታዎች ላይ ተወያይተን ግልጽነት ፈጥረናል ብለዋል።

በዓለም አቀፍም ሆነ በሀገር ደረጃ እየተከሰቱ ያሉ የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግሮች የጥሬ ገንዘብ እጥረት እንዲኖር ተጽዕኖ እያሳረፉ ይገኛሉ ያሉት አስተያየት ሰጪዎቹ ኑሮ ውድነትና ሰላም ላይ የሚመለከታቸው አካላት በትኩረት እንዲሠሩ ጠይቀዋል።

በፋይናንስ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የገቢ ተቋማት ቋቶችን ለይተውና የአሰባሰብ ሥርዓታቸውን አዘምነው ጠንክሮ መሥራት እንደሚጠበቅባቸው አሰተያየት ሰጪዎቹ አንስተዋል።

የጌዴኦ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ኃላፊ አቶ ግርማ ጤካሞ እንደገለጹት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የጥሬ ገንዘብ ጉድለት ከመኖሩ የተነሳ ከተገልጋዮች እየተነሱ ባሉ ቅሬታዎች ተነጋግረን ተግባብተናል።

ሀገራችን ወጪን በውስጥ ገቢ ለመሸፈን በርካታ ሥራዎችን እየሠራች ያለችበት ወቅት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ዞኑም ገቢን አሟጦ ለመሰብሰብ ሁላችንም በባለቤትነት ስሜት ተቀናጅተን መንቀሳቀስ ይኖርብናል ብለዋል።

በያዝነው በጀት ዓመት ላይ በፋይናንስ ያሉ ጉድለቶችን እንደ ጌዴኦ ዞን ለመሙላት ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ እንደሚጠበቅባቸው የተናገሩት አቶ ግርማ በዞን ማዕከል ብቻ እየገጠሙ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት በየወሩ ከ13 ሚሊዮን በላይ ከውስጥ ገቢ መሰብሰብ እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል።

በፋይናንስ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሰዋሉ ባሉ ችግሮች ላይ ተገልጋዩ ህብረተሰብ ጉዳዮችን ማወቁ የጋራ መፍትሔ ለመፈለግ ያለው አሰተዋጽኦ የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ ተሰፋዬ ጎበና – ከፍስሃገነት ጣቢያችን