አከባቢን ለማልማት እጅ ለእጅ መያያዝ እንደሚጠበቅ ተመላከተ

ሀዋሳ፡ ጥቅምት 13/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኮሬ ዞን የማልማት ዕቅድ ዙሪያ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የውይይት መድረክ በኬሌ ከተማ በተካሄደበት ወቅት አከባቢን ለማልማት እጅ ለእጅ መያያዝ እንደሚጠበቅ ተመላክቷል።

የውይይቱን ሰነድ ያቀረቡት የሀብት አሰባሰብ ኮሚቴ አቶ ዮሐንስ ኃይሉ እንደገለጹት፤ ዞኑን ለማልማት በአጭርና በረጅም ጊዜ ዕቅድ የተያዘ ሲሆን በ2016 የበጀት ዓመት ለመሥራት ከታቀዱት ባለሰንሰለት እስካባተርና ዶዞር ግዥ እና ከአልፋጮ ነጭ ሣር ወደ አርባ ምንጭ የሚወስደው መንገድ ሥራ ተጠቃሾች ናቸው።

በቀጣይም 5 ዓመት ዕቅድ ውስጥ 2 የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች በ2ቱ ወረዳ መገንባትና ነባሩን ሆስፒታል ወደ አጠቃላይ ለማሳደግ ግብ መጣሉን ከሪፖርቱ አይተናል።

ዞኑን ማልማት የሚችለው ማህበረሰብ እንደሆነ የገለጹት የኮሬ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ ከህብረተሰቡ ጋር በመወያየትና ምክረ-ሃሳብ ተቀብሎ መተገበር ለዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ተናግረዋል::