ትምህርትን ከጅምሩ ጠንክሮ በመማር የነገን ህይወት የተሻለ ማድረግ እንደሚገባ በሆሳዕና ከተማ የአልበርት አካዳሚ የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ተናገሩ

አልበርት አካዳሚ  በ2015 የትምህርት ዘመን  በክልል አቀፍ ካስፈተናቸው የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች መካከል 93 ከመቶ ወደቀጣይ ክፍል ለማለፍ ችለዋል።

የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ትምህርት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ ዘመድኩን በበኩላቸው በከተማ አስተዳደሩ በ2015 የትምህርት ዘመን የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ከወሰዱ 3ሺህ 1መቶ 48 ተማሪዎች መካከል 38 በመቶ ብቻ ማለፋቸውን ጠቁመው ይህም በዘርፉ ብዙ መሰራት እንዳለበት ጠቋሚ ነው ብለዋል።

በሌላ በኩል ያስፈተኗቸውን ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ያሰለፉ ትምህርት ቤቶች ሊበረታቱ ይገባል ያሉት ኃላፊው አልበርት አካዳሚም ከነዚህ መካከል አንዱ ስለመሆኑም ገልጸዋል።

የትምህርቱን ዘርፍ ስብራት ለመጠገን በተያዘው የትምህርት ዘመን በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው ያሉት አቶ አዳነ በተለይ የትምህርት ባለድርሻ አካላት ለዘርፉ ለውጥ የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

የአልበርት አካዳሚ መስራችና ስራ አስኪያጅ አቶ ግርማ ሞሎሮ ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ ከቅድመ መደበኛ ደረጃ አንስቶ በትኩረት እንደሚሰራ ገልፀዋው ጥሩ ውጤት ለማምጣት የትምህርቱ ባለድርሻ አካላት ትኩረት እንደሚያስፈልግም አመለክተዋል።

ተማሪ ሞላልኝ ኢዮብ በአካዳሚው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ በሊች ጎጎ አዳሪ ልህቀት ትምህርት ቤት ለመማር ካለፉ ተማሪዎች መካከል አንዱ ሲሆን ለውጤቱ ማማር ከግል ጥረቱ ባለፈ የመምህራንና የወላጆቹ አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልጾ።

በአካዳሚው ያነጋገርናቸው የዘንድሮ የ8ኛ ክፍል ተማሪዎችም ካለፉ ተማሪዎች ለውጤታማነታቸው የሄዱበትን መንገድ በመከተል የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

የአካዳሚው መምህራን በበኩላቸው የተማሪዎችን ውጤት የበለጠ ለማሻሻል እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ ኤርጡሜ ዳንኤል – ከሆሳዕና ጣቢያችን