በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮንሶ ዞን የኮልሜ ወረዳ ምስረታ ተካሄደ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮንሶ ዞን የኮልሜ ወረዳ ምስረታ ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 05/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮንሶ ዞን የኮልሜ ወረዳ ምስረታ በዓል በደልቤና ከተማ ተካሂዷል።

በወረዳው ምስረታ በዓል ላይ የአዲሱ ኮልሜ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በርግላንድ ላቀው፥ በየደረጃ   ባሉ ም/ቤቶች ፀድቆ በክልሉ መንግስት ጥያቄው ተቀባይነት አግኝቶ ምላሽ በመሰጠቱ ደስተኛ መሆናቸውን ገልፀዋል።

በህዝብ ተሳትፎና ትብብር የተገኘውን ወረዳ የመሆን ጥያቄ ምላሽ በመጠቀም የወረዳው ህዝብ ለጋራ ዓላማና ግብ መስራት እንደሚገባው አስገንዝበዋል።

የወረዳው ህዝብ በሰላማዊ መንገድ ላቀረበው ጥያቄ ተገቢ ምላሽ እንዲያገኝ መደረጉን ያደነቁት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በም/ል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ዓለማየሁ ባውዲ ናቸው፡፡ የተጀመሩ የአካባቢ ልማትና ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማስቀጠል በወንድማማችነትና እህትማማችነት የተመሰረተውን ወረዳ ልማት ማስቀጠል እንደሚገባ ገልፀዋል።

ለአዲሱ ክልል ዕድገት ሰላም አስፈላጊ ነው ያሉት የደቡብ ኢትዮጵያ የመንግስት ምክትል ዋና ተጠሪ ዳዊት ገበየሁ ከአጎራባችና ሌሎች ህዝቦች ጋር የሚያጋጥሙ ችግሮችን በዉይይት በመፍታትና በጋራ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል።

ከምስረታው ጎን ለጎን የወረዳው አስተዳደር መስሪያ ቤት ተመርቋል።

በምስረታው ላይ የተገኙት የኮልሜ ከተማ ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት ጥያቄያቸውን በሰላማዊ መንገድ ማቅረባቸውን ተከትሎ ባገኙት ምላሽ መደሰታቸውን ገልፀው፥ ለክልሉና ለዞኑ አስተዳደር ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ዓለማየሁ ባውዲ እና አቶ ዳዊት ገበየሁ ም/ል የመንግስት ዋና ተጠሪ፥ የክልሉ የፍትህ አመራሮች፣ የኮንሶ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪና ከፍተኛ የዞኑ አመራሮች እና የወረዳው ነዋሪዎች ተሳታፊ ሆነዋል።

ዘጋቢ፡ ብዙነሽ ዘውዱ