በጎፋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ1 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብስቡን የዞኑ ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

በጎፋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ1 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብስቡን የዞኑ ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

‎የ2018 ግብር አሰባስብ እና የንግድ ሥራ ፈቃድ ዕድሳት ሥራዎች ዙሪያ የንቅናቄ መድረክ በሳውላ ከተማ ተካሂዷል።

‎የጎፋ ዞን ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ሙሉቀን ጉጃ፤ በበጀት ዓመቱ የገቢ አሰባስብ ሂደት ፍትሃዊና ግልጽ ለማድረግ ከወረቀት ወደ ዲጂታል በማሳድግ በርካታ ሥራዎች መሰራቱን ገልጸዋል።
ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ሀብት ሙሉ በሙሉ በመሰብሰብ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች መመለስ እንደሚገባ ገልጸዋል።

‎በ2018 የግብር ዘመን ከዚህ ቀደም በሶስት ደረጃ የነበረው የግብር ከፋይ ምደባ ወደ በሁለት ደረጃዎች ብቻ ተቀይሮ 487 የደረጃ “ሀ” እና 10 ሺህ 563 የደረጃ “ለ” ግብር ከፋዮች እንዳሉ ጠቁመው ቀሪውን 25 በመቶ የገቢ አሰባሰብ በትኩረት የሚሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

‎በመድረኩ ላይ የተገኙት የጎፋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ሥራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ ምናሴ ኤልያስ፤ ‎ዞኑ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚያስገኙ ምርቶች በስፋት የሚገኙበት በመሆኑ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ሀብት ለመሰብሰብ በትኩረት በመስራት የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል።

‎ገቢ በአግባቡ መሰብሰብ የልማት ዋና አንቀሳቃሽ ኃይል በመሆኑ ዘርፉ ለገቢ መዋቅሮች ብቻ የሚተው እንዳልሆነ አጽንኦት ሰጥተዋል።

‎የአፈጸጸም ሪፖርት ያቀረቡት የጎፋ ዞን ገቢዎች የታክስ ኦፕሬሽን ዳይሬክቶሬት አስተባባሪ አቶ ቴዎድሮስ ገነነ በበኩላቸው፤ በበጀት ዓመቱ የገቢ አማራጮች በመጠቀም ከ2 ቢሊዮን 91 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ 1 ቢሊዮን 851 ሚሊዮን ብር በላይ መስብስብ መቻሉን ገልጸዋል።

‎የውይይቱ ተሳታፊዎች ዲጂታል የክፍያ ስርዓትን በመጠቀም ሌብነትና ብልሹ አስራርን ለመከላክልና የገቢ አሰባሰቡን በማዘመን የህዝቡን የመልማት ጥያቄ ለመመለስ መሰራት እንዳለበት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል ።
‎ዘጋቢ፡ ስንታየሁ ሙላቱ – ከሣውላ ጣቢያችን