የጉራጌ ማህበረሰብ ባህላዊ እሴቶች ሳይበረዙ ለትውልድ ለማስተላለፍ የኪነ ጥበብ ዘርፉን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝ የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ

የጉራጌ ማህበረሰብ ባህላዊ እሴቶች ሳይበረዙ ለትውልድ ለማስተላለፍ የኪነ ጥበብ ዘርፉን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝ የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ

በመምሪያው አዘጋጅነት “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል የኪነ ጥበብ ምሽት በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል።

የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ መሰረት አመርጋ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ የጉራጌ ማህበረሰብ ነባር ባህሎች ሳየበረዙ ለትውልድ እንዲሸጋገሩ ለማስቻል የኪነ ጥበብ ዘርፉን በማጠናከር ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል።

ኪነ-ጥበብ የአንድን ማህበረሰብ ታሪክ፣ ባህል፣ ቋንቋና የአኗኗር ስርዓት ለቀጣይ ትውልድ የሚተላለፍበት መሳሪያ በመሆኑ ዘርፉን በመጠቀም ልዩ ልዩ ተግባራት በመከናወን ላይ ይገኛሉ ብለዋል።

ታሪኩን የሚያውቅ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ኪነ-ጥበብ ትልቅ ድርሻ አለው ያሉት ኃላፊዋ፤ ማህበረሰቡም ባህሉንና ስርዓቱ እንደተጠበቀ ለትውልድ የማሻገር ሀላፊነት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

ዶክተር ድርሻ ደማም፣ ሂክማ ሰፋ እንዲሁም ሻምበል ቅድስት ትዕዛዙ እና አርቲስት ሙባረክ ኡመር የኪነ ጥበብ ምሽቱ ተሳታፊዎች ናቸው፡፡ በሰጡት አስተያየት ኪነ-ጥበብ የተደበቁ ነባር የማህበረሰቡ ባህላዊ እሴቶች አውጥቶ ለሌሎች ለማሳወቅና ለማስቀጠል ከፍተኛ አቅም እንዳለው ገልጸዋል።

አንድ ማህበረሰብ የሌላውን ባህል የሚያከብረው የራሱን ባህል አክብሮና ጠብቆ ሲይዝ በመሆኑ ባህላዊ እሴቶችን መጠበቅ እንደሚገባ አስረድተዋል።

ተሳታፊዎቹ አክለውም የኪነጥበብ ምሽቱ በርካታ በመዘናጋት የተረሱ ባህላዊ እሴቶች የሚቀርቡበት በመሆኑ ማህበረሰቡ ባህላዊ እሴቱ ያለበት ደረጃ ለመገምገም መሳተፍና ባህሉን መልሶ ማጠናከር እንዳለበት ጠቁመዋል።

የጉራጌ ማህበረሰብ ባህልና ቋንቋ እንዲሁም የአኗኗር እሴቱ በኪነ ጥበብ መድረኮች ሳይወሰን ተሰንዶ ለቀጣይ ትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባም ጠቁመዋል።

ዘጋቢ፡ አዱኛ ትዕዛዙ – ከወልቂጤ ጣቢያችን