‎ከተረጂነት በመውጣት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ የሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም መሸፈን እንደሚገባ ተገለጸ

‎ከተረጂነት በመውጣት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ የሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም መሸፈን እንደሚገባ ተገለጸ

‎በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ “ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለተሟላ ሀገራዊ ክብር እና ሉአላዊነት” በሚል መሪ ቃል የውይይት እና ከየቀበሌያት የተሰበሰቡ እህል እና ቁሳቁስ ለወረዳው አስተዳደር ገቢ ተደርገዋል።

‎ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚለው መርህ ትኩረት ተሰጥቶ በመሠራቱ ውጤታማ በመሆን ማህበረሰቡ ራሱን ችሎ ለሰብአዊ ድጋፍ የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል።

‎በዞን ደረጃ ለመሰብሰብ አቅደን የጀመርነው 72 ሚሊዮን መጠባበቂያ ፈንድ በይርጋጨፌ ወረዳ በእህል እና በቁሳቁስ መልክ የተጀመረው የማሰባሰቡ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል ሲሉ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) ተናግረዋል።

‎ይህም በሀገር አቀፍ ደረጃ ለተጀመረው ሥራ እያንዳንዱ አመራር ህብረተሰቡን በማንቀሳቀስና ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ተግባሩ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረግ ይጠበቅበታል ብለዋል።

‎የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ፤ በወረዳው ባሉ ሁሉም ቀበሌያት ህብረተሰቡ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የሚለውን ሀሳብ ተቀብሎ በመሥራት
‎አሁን ላይ ለሰብዓዊነት ከየቀበሌው እህል በመሰብሰብ በወረዳ ማዕከል የማስረከቡ ሥራ ተሠርቷል ሲሉ ተናግረዋል።

‎በቀጣይም በሰብአዊነት ራሳችንን ለመቻል የጀመርነውን ሥራ አጠናክረን ከማስቀጠልም ባሻገር በእያንዳንዱ ቀበሌ ያለው ማህበረሰብ ሠርቶ ምርታማ እንዲሆን በማድረግ ከተረጂነት መንፈስ ነፃ እና ራሱን የቻለ ማህበረሰብ መፍጠር ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል።

‎ከተሳታፊዎች መካከል አርሶአደር አክሊሉ ወብዩ እና ጴጥሮስ በዳሶ፤ በቀበሌያቸው ከተረጂነት ለመውጣት በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ የሚጠበቅበትን እህል በማዋጣት በወረዳ ደረጃ እንድናስረክብ ተደርጓል ብለዋል።

‎በመጪው ጊዜያትም ህብረተሰቡም ሆነ እኛ በግላችን ባለን ማሳ ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ትኩረት ሰጥተን በመሥራት የሰብአዊ ድጋፉን እናስቀጥላለን ሲሉ አስረድተዋል።

‎ዘጋቢ፡ አብዶ አያላ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን