በኢንተርፕራይዝና ኢንቨስትመንት የልማት ስራዎች ላይ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉ ተገለጸ

በኢንተርፕራይዝና ኢንቨስትመንት የልማት ስራዎች ላይ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 19/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በወረዳው በበጀት አመቱ በኢንተርፕራይዝና ኢንቨስትመንት የልማት ስራዎች ላይ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን በጉራጌ ዞን የእዣ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ፡፡

የእዣ ወረዳ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ፅ/ቤት በ2018 በጀት ዓመት የተከናወኑ የልማት ተግባራት ጉብኝት አካሂዷል።

የእዣ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ዘውዱ ዱላ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፥ በወረዳው በበጀት አመቱ በኢንተርፕራይዝና ኢንቨስትመንት የልማት ስራዎች ላይ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቁመው፥ የሚዲያ ተቋማት መሰል የልማት ስራዎች ለህብረተሰብ ከማሳወቅ ባሻገር በማንቃት ጭምር የድርሻቸውን መወጣት እናዳለባቸው አስረድተዋል፡፡

በወረዳው 43 ኢንቨስተሮች በስራ ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፥ አዳዲስ ወደስራ የሚገቡ ኢንቨስተሮች ስራ እንዲጀምሩ ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ ስለመሆኑም አመላክተዋል።

ቪታ ሳሉታ የመሳሰሉ ኢንቨስትመንቶቹ አካባቢን ለውጠው የውጭ ምንዛሪ በማስገኘትና ለዜጎች የስራ እድል በመፍጠሩ ተግባር ያላቸው ተሞክሮ ለማስፋት ያለመ ጉብኝት መሆኑንም ጠቁመው፥ እነዚህ የተጎበኙ የልማት ስራዎች የወረዳውን ገቢ በማሳደግ ከ5 ዓመት በፊት የነበረው ዓመታዊ የወረዳው ገቢ ከ67 ሚሊየን ወደ 325 ሚሊየን ያደረሰ መሆኑንም አመላክተዋል።

የእዣ ወረዳ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ፅሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ አሸናፊ በቀለ በበኩላቸው የስራ ጉብኝቱ በየተቋማት የተከናወኑ ተግባራት በሪፖርት ከመግለፅ ባሻገር ተግባሩ በአካል በማየት ለማረጋገጥና ልምድ ለመውሰድ ሲያግዝ፥ ተግባራቸው የሚጎበኝላቸው አካላትን የማነቃቃት አስተዋፅኦው ከፍተኛ ነው ብለዋል።

በተጎበኙት ወቅት የተስተዋሉ ውስንነቶችም የሚመለከታቸው ተቋማት ችግሮቹን እንዲፈቱ እንደሚያግዝ ጠቁመው፥ የወረዳው አመራርና አስተባባሪ አካላት የተግባሩ ጠቀሜታ በመረዳታቸው ለዘርፉ እገዛ በማድረግ፥ በተለያዩ የሚዲያ አማራጮች የተከናወኑ ተግባራት ለማህበረሰቡ ተደራሽ እንዲሆንና ተሞክሮዎች እንዲሰፉ አስችሏል ነው ያሉት ።

ከጉብኝቱ ተሳታፊዎች መካከል ወ/ሮ ዙርያሽ ማሬና ደሳለኝ ከበደ እንደገለፁት የስራ ጉብኝቱ እንደመንግስት ለህብረተሠቡ የኑሮ ውድነት ለመቀነስና የተሻሻለ ሕይወት እንዲኖረው ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት በሁሉም ቀበሌ ለማስፋት ልምድ የተወሰደበት ነው ብለዋል።

ተግባራቸው የተጎበኘላቸው ኢንተርፕራይዞችና ኢንቨስትመንቶችም እየተደረገላቸው ባለው ድጋፍ አመስግነው ሊሟሉላቸው የሚገቡ ጉዳዮችም አሳውቀዋል።

ዘጋቢ፡ አማረ መንገሻ – ከወልቂጤ ጣቢያችን