የብራይት ፕሮጀክት የሴቶችንና ህፃናትን የስራ ጫና ከማቃለል ባሻገር የንፁህ መጠጥ ውሀ ተደራሽነት ላይ የሚመታይ ተግባር ማከናወኑን የጋሞ ዞን ውሀና ኢነርጂ መምሪያ አስታወቀ

የብራይት ፕሮጀክት የሴቶችንና ህፃናትን የስራ ጫና ከማቃለል ባሻገር የንፁህ መጠጥ ውሀ ተደራሽነት ላይ የሚመታይ ተግባር ማከናወኑን የጋሞ ዞን ውሀና ኢነርጂ መምሪያ አስታወቀ
‌‎
‎በጋሞ ዞን ዲታ ወረዳ በብራይት ፕሮጀክት በ2.1 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የንፁህ መጠጥ ውሀ ፕሮጀክት ተመርቋል፡፡

‎ፕሮጀክቱ 1 ሺህ 482 ነዋሪዎችን ቀጥታ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ተጠቁሟል።

‎ከቀበሌው ነዋሪዎች መካከል ወ/ሮ አሰለፈች ዋሻ እና አቶ ኤሊያስ ኤንተሎ በውሀ እጦት ለበርካታ አመታት በውሀ ወለድ በሽታ ሲሰቃዩ እንደነበር አውስተው የፕሮጀክቱ እውን መሆንና ለአገልግሎት መብቃቱ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንደሚኖረው አብራርተዋል።

‎ነዋሪዎቹ የእለት ተእለት ኑሮን ለመግፋት ንፁህ የመጠጥ ውሀ ወሳኝ መሆኑን የገለፁት ነዋሪዎቹ የብራይት ፕሮጀክት ላከናወነው ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

‎የዶቃማ ቀበሌ ስራ አስኪያጅ አቶ ያሬድ ዴብሳ፤ ከዚህ ቀደም ህብረተሰቡ በንፁህ መጠጥ ውሀ እጦት ይቸገር እንደነበር አውስተው፤ በቀበሌው ከሚገኙ 1032 አባወራምች 249ኙ የንፁህ መጠጥ ውሀ ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውንም አብራርተዋል።

የዲታ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የውሀ እና ኢነርጂ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ‎አቶ ኡታ ጌቱ፤ በወረዳው የንፁህ መጠጥ ውሀ ሽፋን 39 ከመቶ መድረሱንና ዛሬ በብራይት ፕሮጀክት የተከናወነው የውሀ ግንባታ ሽፋኑን ከፍ ከማድረጉም ባሻገር ለቀበሌው ማህበረሰብ የተለየ ፋይዳ እንዳለው ጠቁመዋል።

‎የዲታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አሸናፊ ኦይዳ(ዶ/ር)፤ ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በወረዳው ለውጦችን ለማስመዝገብ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን አብራርተው የንፁህ መጠጥ ውሀ ተደራሽነት ክፍተትን ለመሙላት ብራይት ፕሮጀክት ያደረገው ጥረት በወረዳው ተጨባጭ ለውጥ እንዲመዘገብ አስተዋፅኦ እያበረከተ መገኘቱን መስክረዋል።

‎ብራይት ፕሮጀክት በወረዳው የሚገኙ የልማት ክፍተቶችን መሰረት አድርጎ በርካታ ስራዎችን መስራቱን ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ የተመረቀውን የንፁህ መጠጥ ውሀ ፕሮጀክት መጠበቅ እንዳለበት አሳስበዋል።

‎የጋሞ ዞን ውሀና ኢነርጂ መምሪያ ኃላፊ ተወካይ አቶ መሰለ አይናለም፤ የብራይት ፕሮጀክት በጋሞ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች የሴቶችንና ህፃናትን የስራ ጫና ከማቃለል ባሻገር በንፁህ መጠጥ ውሀ ተደራሽነት በማረጋገጥ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል።

‎አክለውም ውሀ የሚባክን፣ የሚያልቅና የሚጠፋ በመሆኑ የግልና የአካባቢን ጤንነት ከመጠበቅ ባሻገር የተጠናከረ የአፈርና የውሀ ጥበቃን ማድረግ ይገባል ብለዋል።

‎የብራይት ፕሮጀክት አስተባባሪ ይልቃል አንተነህ(ዶ/ር)፤ የተፋሰሱን ነዋሪዎች የኑሮ ደረጃ ለማሻሻልና የነዋሪውን ኢኮኖሚ መገንባትን ትኩረት አድርጎ በ2.1 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የንፁህ መጠጥ ውሀ ፕሮጀክት መገንባቱን ገልጸዋል በቀጣይም ሌሎች የውሀ ተቋማት እንደሚገነቡም ቃል ገብተዋል።

‎የፕሮጀክት አስተባባሪ፤ የብራይት ፕሮጀክት 1 ሚሊየን 550 ሺህ ብር ፤ 550 ሺህ ብር ደግሞ በህብረተሰብ ተሳትፎ ወጪው መሸፈኑን ተናግረው ዛሬ የተገነባውን የንፁህ መጠጥ ውሀን ፕሮጀክት እውን እንዲሆን በቅንነትና በባለቤትነት ለተንቀሳቀሱ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

‎ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን