በጎፋ ዞን መሎ ኮዛ ወረዳ ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ለሚገነባው የእንስሳት ግብይት ማዕከል ግንባታ የሳይት ርክክብ ተደረገ

በጎፋ ዞን መሎ ኮዛ ወረዳ ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ለሚገነባው የእንስሳት ግብይት ማዕከል ግንባታ የሳይት ርክክብ ተደረገ

‎ፕሮጀክቱ በጥራትና በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ የዞኑ አስተዳደር ከወረዳው ጋር በመሆን አስፈላጊውን የድጋፍና ክትትል የሚያደርግ መሆኑን የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ሚናሴ ኤልያስ ተናግረዋል።

ምክትል አስተዳዳሪው እንደገለጹት፤ መንግስት በትኩረት ከሚሰራባቸውና ለገቢ ምንጭ ሞተር ከሆኑ ተግባራት አንዱ የንግድ ስርዓቱን ማዘመን በመሆኑ የሳይት ርክክቡ ዘመናዊ የእንሰሳት ግብይት እንዲኖር ለማድረግ ነው።

‎የመሎ ኮዛ ወረዳ ምክትል አሰተዳዳሪና የጤና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መርዶክዮስ ማርቆስ በበኩላቸው፤ በወረዳው የአርሶአደሩን ኑሮ ለማሻሻል በFSRP ፕሮግራም በጀት ድጋፍ በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን ተናግረዋል።

‎ዛሬም በFSRP ፕሮግራም በጀት ድጋፍ በጋይሳ ቀበሌ የክላስተር ቀበሌያትን ተጠቃሚ የሚያደርግ ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጭ የእንሰሳት ግብይት ማዕከል ግንባታ ማስጀመር መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ።

‎የወረዳው የግብርና ጽህፈት ቤት የFSRP ፕሮግራም የፕሮጀክት አስተባባሪ ኢንጂነር ታሪኩ ሻትንሳ በበኩላቸው፤ የጋይሳ የዘመናዊ እንስሳት ግብይት ማዕከል ግንባታ ለአካባቢው ማህበረሰብ ትልቅ ዕድል መሆኑን ተናግረዋል።

‎የፕሮጀክቱ ጠቅላላ ዋጋ 22 ሚሊዮን 723 ሺህ ብር በላይ ሲሆን በውስጡ የግብይት ማዕከል ዙሪያ አጥር ግንብ፣ የቀረጥ ቢሮ /Tax room/፣ የህክምና ክፍል፣ የጥበቃ ቤት ሼድ ግንባታ፣ መጫኛ(Loading ramp)፣ መፀዳጃ ቤት፣ የውሃ ታንኬር ግንባታ፣ ቆሻሻ ማስወገጃ፣ የከብቶች ማዳቀያ በረት ግንባታን ጨምሮ ሌሎች ስራዎችንም መያዙን አብራርተዋል።

‎የፕሮጀክቱን ግንባታ ስራ በጨረታ ያሸነፈው ኮንትራክተር ንጋቱ ዴና በበኩላቸው፤ የግንባታውን ስራ በጥራትና በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በትኩረት የሚሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

‎ዘጋቢ፡ ስንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን