የማንቸስተር ሲቲ አዲስ መሪ ታውቋል!

የማንቸስተር ሲቲ አዲስ መሪ ታውቋል!

የፔፕ ጋርዲዮላን ታላቅ አሻራ ተከትሎ፣ የሲቲን መንበር ለመረከብ የተመረጠው ስም ይፋ ሆኗል – ኤንዞ ማሬስካ!

ጣሊያናዊው አሰልጣኝ ማሬስካ ከማንቸስተር ሲቲ ጋር የቃል ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ፋብሪዚዮ ሮማኖ ዘግቧል።

ማሬስካ ሁልጊዜም ቢሆን የፔፕ ጋርዲዮላን የፍልስፍና አምድ ሊያስቀጥል የሚችል ቁጥር አንድ እጩ ተደርጎ ሲታጭ የቆየ ሰው ነው።

 የ44 ዓመቱ አሰልጣኝ የሲቲን የጨዋታ ዘይቤ ጠንቅቆ ያውቃል።ቀደም ሲል በኤቲሃድ የፔፕ ረዳት የነበረ መሆኑ አይዘነጋም።

 በክለቡ አስተዳዳሪዎች ዘንድ የጋርዲዮላን ዘመናዊ የእግር ኳስ አብዮት ያለምንም እንከን ለማስቀጠል ፍጹም ተመራጭ ሆኖ ተገኝቷል።

እንደ መረጃዎች ገለጻ ከሆነ፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለው ስምምነት ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀ ሲሆን ማሬስካ በኢትሃድ ለሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት የሚቆይ የመጀመሪያ ኮንትራት ይፈርማል።

በእግር ኳስ ዓለም ታላላቅ አሰልጣኞችን መተካት ሁልጊዜም ከባድ ፈተና ነው።

ጋርዲዮላ ያስቀመጠው መስፈርት እጅግ በጣም ከፍ ያለ ቢሆንም፣ ማሬስካ ግን የፔፕን ‘ታክቲካዊ ዲ ኤን ኤ’ የተጋራ በመሆኑ፣ ይሄንን ከባድ ሃላፊነት ለመሸከም ትክክለኛው ሰው ሊሆን ይችላል።

ሰማያዊዎቹ የማንቸስተር ክፍሎች አዲስ ምዕራፍ ሊጀምሩ ዋዜማ ላይ ናቸው።

ዘጋቢ ፡ ሙሉቀን ባሳ