ለክብሩ የሚጫወት ታጋይ

ለክብሩ የሚጫወት ታጋይ

በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ኦልድ ትራፎርድን እንደሚለቅ በይፋ ያረጋገጠው ብራዚላዊው ኮከብ ካሴሚሮ፣ በሜዳ ላይ እያሳየ ያለው ድንቅ ብቃት “የመጨረሻ ዳንስ” (The Last Dance) አስመስሎታል።

ክለቡን እንደሚለቅ መታወቁ ለብቃቱ መውረድ ምክንያት መሆን ሲገባው፤ ካሴሚሮ ግን በተቃራኒው ወደ ቀድሞው የማሸነፍ ጥማቱ ተመልሷል።

ካሴሚሮ ማንቸስተር ዩናይትድን እንደሚለቅ ካሳወቀ በኋላ፣ በተለይም ካለፉት ጥቂት ሳምንታት ወዲህ በሜዳ ላይ ያለው ተጽዕኖ በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

ብዙዎች “በቃው” ብለው በደመደሙበት ወቅት፣ እርሱ ግን በታላቅ ጨዋነትና ሙያዊ ብቃት ክለቡን ወደ ቻምፒዮንስ ሊግ ለመመለስ በቁርጠኝነት እየተጫወተ ይገኛል።

ጨዋታዎችን የማንበብ እና የተቃራኒ ቡድንን ጥቃት ቀድሞ የማቋረጥ ብቃቱ ወደ ቀድሞው ጥንካሬው ተመልሷል።

ወጣቶቹን ተጫዋቾች በማበረታታት እና በመምራት ረገድ ያለውን ሚና አጠናክሯል።

ብዙ ተጫዋቾች መልቀቃቸው ሲረጋገጥ ትኩረታቸው ወደ ቀጣዩ ክለባቸው ያደላል፤ ካሴሚሮ ግን ለማንቸስተር ዩናይትድ ማሊያ ያለውን ክብር በተግባር እያሳየ ነው። ደጋፊዎች በሜዳ ላይ ያለውን ትጋት እያዩ “ስንብቱ ይቆጨናል” በሚል ስሜት እንዲሸኙት እያደረገ ይገኛል።

ካሴሚሮ እየተጫወተ ያለው ለመልቀቅ ሳይሆን፣ የታሪክ አካል ሆኖ ለማለፍ ይመስላል።

በኦልድ ትራፎርድ የቆየባቸውን የመጨረሻ ቀናት በውጤትና በክብር ለማጀብ የወሰነ ታላቅ ተጫዋች ነው።

ማንቸስተር ዩናይትድ ቻምፒዮንስ ሊግ ለመግባት ከሚያስፈልገው 1 ነጥብ ጀርባ የካሴሚሮ አስተዋጽኦ የማይናቅ ነው።

ብራዚላዊው አማካይ ክለቡን የሚለቀቀው በሽንፈት ሳይሆን፣ ዩናይትድን ወደ ታላቁ አውሮፓ መድረክ በመመለስ እንደ ስጦታ ሊያበረክትላቸው ጫፍ ላይ ደርሷል።

ይህ የካሴሚሮ ስንብት በዩናይትድ ታሪክ ውስጥ በክብር የሚታወስ ይሆናል።

ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ