ባለፉት ዘጠኝ ወራት 5.5 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች ወደስራ መግባታቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ
በሮው በክልሉ እየተከናወኑ ያሉ የኢንቨስትመንት ተግባራትን ባለድርሻ አካላት እና መንግስታዊ ያልሆኑ አጋር ድርጅቶች በተገኙበት ገምግሟል፡፡
በክልሉ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማበረታታት ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባለፈ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ የደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ንግድ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ እና የኢንቨስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከበደ ተስፋዬ ተናግረዋል።
በተለይም አዲሱ ክልል እንደ ክልል ከተደራጀ በኋላ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ እየተሳለጠ ነው ያሉት አቶ ከበደ፤ በቀድሞ ክልል እያለ የነበረው የኢንቨስትመንት አሀዝ 655 ከነበረበት አሁን ወደ 1063 አሀዝ ማደጉንም ጠቁመዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራትም 5.5 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች ወደስራ መግባታቸውን የተናገሩት አቶ ከበደ፤ ከሰባት ሺ ሄክታር በላይ መሬት ተረክበው ወደስራ መግባታቸውንም ተናግረዋል።
ክልሉ በግብርና ዘርፍ በተለይም በቡና፣ በቅመማ ቅመም እንዲሁም በሰብል ልማት ምቹ ስነ-ምህዳር ያለው መሆኑን ተናግረው፤ ያለውን የምርት አቅርቦት ወደ ማኒፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ከመቀየር አንጻር ውስንነት መኖሩንም ገልጸዋል።
ለዚህም በክልሉ በሚገኙ ስድስት ዞኖች ኢንዱስትሪዎችን ለመገንባት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ሲሆኑ ባለሀብቱም በዚሁ ዘርፍ እንዲሰማራ ጥሪ አቅርበዋል።
በተለይም ከዚህ ቀደም ይነሱ የነበሩት የመብራት፣ የቴሌኮም እና የመንገድ ችግሮች እየተቀረፉ መሆኑንም በመጠቆም።
ባለሀብቱ ለአካባቢ ማህበረሰብ የቴክኖሎጂ ሽግግር ከማድረግም አንጻር አንድ ሺ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ያደረጉ ሲሆን 75 ኪሎ ሜትር መንገዶች ማከናወናቸውን ጠቅሰዋል።
ከክልሉ ንግድ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ጋር ተቀናጅተው ከሚሰሩ መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ የላንድፎር ላይፍ ፕሮጀክት ዳይሬክተር አቶ ፍቅሩ ታከለ በበኩላቸው፤ በመንግስት በባለሀብቱ እንዲሁም በአርሶአደሩ መካከል ያለውን ግንኙነት በማጠናከር ከአርሶ አደሩ የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት በቅንጅት እየሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል።
ከሸካ፣ ከቤንች ሸኮ፣ ከምእራብ ኦሞ ዞን ንግድ እና ኢንቨስትመንት መምሪያ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ሀላፊዎች እና ባለሙያዎች መካከልም አቶ ስንታየሁ ካርካ እና አቶ ኑሩ ኢብሪሂም እንዲሁም አቶ አንዱአለም ሻጫቸው በበኩላቸው፤ ለውጡ እንደ ክልል ከመጣ በኋላ በየዞኖቹ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው እየተሳለጠ መሆኑን ተናግረዋል።
በየዞኖቹ በተለይም በግብርና ዘርፍ መሬት ተረክበው በሙሉ አቅማቸው እያለሙ ያሉ ባለሀብቶች እንዳሉ ሁሉ በሙሉ አቅማቸው ያልገቡ መኖራቸውን ጠቅሰው፤ የመለየት እና ችግራቸውን የመቅረፍ ስራ ይሰራልም ብለዋል።
ባለሀብቱም የአካባቢው ማህበረሰብን በቴክኖሎጂ ከመደገፍ ባለፈ የጤና፣ የትምህርትና የመንገድ መሰረተ ልማቶችን በመክፈት ጭምር እያገዙ መሆኑ የሚበረታታና ይህም ተጠናክሮ የሚቀጥልበትን መንገድ ማመቻቸት እንደሚገባ ጠቁመዋል።
ዘጋቢ: አብዮት በቀለ – ከሚዛን ጣቢያችን

More Stories
በዳዉሮ ዞን እየተሠሩ የሚገኙ የልማት ሥራዎች ለህዝቡ የመልማት ጥያቄ ምላሽ እያስገኙ መሆናቸዉ ትኩረት ሊደረግባቸው እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን ገለጹ
በዘመናዊ የእንስሳት እርባታ ዘርፍ በመሰማራታቸው የቤት ፍጆታን ከማሟላት ባሻገር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን በጋሞ ዞን ገረሴ ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ አንዳንድ አካላት አረጋገጡ
ክቡር የሆነውን የሰውን ሕይወት ለመታደግ ደም በመለገስ ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ የይርጋጨፌ ከተማ ጤና ጽህፈት ቤት አሳሰበ