ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ

ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ በወቅቱ መያዝ እንደሚጠበቅበት ተገለጸ

የጎፋ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊና በዑባ ደብረ ጸሐይ ምርጫ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ ተወካይ አቶ ጋሻያለሁ ገላ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በሚወዳደሩበት ምርጫ ክልል ካርድ በወሰዱበት ጊዜ እንደገለጹት ሁሉም ሰው ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ በቀጣይ የሚያስተዳድረውን መንግስት መምረጥ እንዲችል የምርጫ ካርድ መያዝ ይጠበቅበታል።

የ7ኛ ሀገራዊ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ በዞኑ በሚገኙ ስድስት የምርጫ ክልሎች በሚገኙ 351 የምርጫ ጣቢያዎች ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን ባለው ቀሪ የምዝገባ ጊዜ ዕድሜው ለመራጭነት የደረሰ ዜጋ ሁሉ አሻራውን በማኖር ህገ መንግስታዊ መብቱን እንዲጠቀም አስገንዝበዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ልዩ አማካሪና የዑባ ደብረፀሐይ የምርጫ ክልል የክልል ምክር ቤት ዕጩ ተወካይ ዶ/ር ቦሻ ቦምቤ በበኩላቸው፥ የዘንድሮ ምርጫ በአይነቱ የተለየና የዴሞክራሲ ምህዳሩን በማስፋት ሁሉንም ማህበረሰብ ተሳታፊ ያደረገ መሆኑን ገልፀዋል።

በዘንድሮ ምርጫ ሁሉም ዜጋ ተሳታፊ መሆን ይጠበቃል ያሉት ዶክተር ቦሻ፥ ምርጫው ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ እንዲሆን በክልሉ መንግስት በቂ ዝግጅት መደረጉን ጠቁመዋል።

ምርጫ መንግስት የሚመሰረትበት ብቸኛ መንገድ በመሆኑ ዜጎች የመምረጥ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ ጠይቀዋል።

ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን