የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ቦታዎች ለምተው የሚፈለገው ውጤት እንዲመዘገብ እንክብካቤ ማድረግና ከንክኪ ነፃ መሆን እንዳለባቸው የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ አሳሰቡ

እንደ ዞን ሥራው በሚተገበርባቸው ወረዳዎች 50 ንዑስ ተፋሰሶችን ተግባራ ለማድረግ በሐመር ወረዳ ላላ ቀበሌ ገማ ዱካ መንደር ማንጊ ተራራ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ላይ በመገኘት ነው የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ይህንን ያሳሰቡት።

የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ጥቅሙን ከአመራሩ ይበልጥ የሥራው ባለቤት የሆነው ህዝቡ ማብራራት የሚችልበት ጊዜ ላይ መድረሱን ዋና አስተዳዳሪው ጠቅሰው፤ በየአካባቢው የሚተገበረው ይህ ሥራ ውጤት እንዲያስመዘግብ በትኩረት ሊሠራ ይገባል ብለዋል።

በመርሐ ግብሩ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ዘርፍ የልማት ሴፍትኔት ፕሮግራም የማህብረሰብ ሥራዎች አስተባባሪ አቶ ኩሴ ቢሴ፤ ከዚህ በፊት የተሠሩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች ለውጥ ማስመዝገባቸውን አስታውሰዋል።

የተተገበሩ ቦታዎች በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በግጦሽ ሳር እና በአካባቢው ምቹ የሆኑ የግብርና ምርቶችን ተግባራዊ ማድረግና መጠቀም ያስፈልጋል ብለዋል አቶ ኩሴ።

በግጦሽ ክለላና በተፋሰስ በአጠቃላይ 7 ሺህ 145 በአፈርና ውሃ ጥበቃ በተለያዩ ስትራክቸሮች ለመተግበር ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ አብራርተዋል።

በወረዳ ደረጃ የሚለማው መሬት በአግባቡ ተጠብቆና እንክብካቤ ተደርጎ ለውጤት እንደሚሠራና በይፋ የተጀመረውን የ2018 ዓ.ም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን በተከታታይነት ለማከናወን ተግተው እንደሚሠሩ የሐመር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሳሙኤል ጋርሾ ገልፀዋል።

በሥራው የተሳተፉ አርብቶ አደሮችም በዘርፉ ተጠቃሚ ለመሆን በቁርጠኝነት እንደሚሠሩና እንክብካቤ ማድረግና ከንክኪ በፀዳ መልኩ ተጠብቆ ለተሻለ ለውጥ ቦታውን እንደሚይዙ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን