በከተማው በተያዘው በጀት ዓመት በ5 ወራት ውስጥ 1 ቢሊየን 5 ሚሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ መቻሉን የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ

‎የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማሳለጥ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱና በታማኝነት እንደሚከፍሉ አንዳንድ የአርባምንጭ ከተማ ነጋዴዎች ተናግረዋል።

‎አንዳንድ የአርባምንጭ ከተማ ነጋዴዎች፤ የአርባምንጭ ከተማን ዕድገት ለመደገፍ እና የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ከዳር ለማድረስ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል ግዴታቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።

‎በግብር አሰባሰብ ሂደት የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችን በማረምና ወቅቱን የጠበቀ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት በቀጣይ መሰጠት እንደሚጠበቅ ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።

‎የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ በረከት ማቲዮስ፤ በ2018 በጀት አመት በ5 ወራት ውስጥ 1 ቢሊየን 5 ሚሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ መቻሉንና የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የተለያዩ ተግዳሮቶች እንደነበሩ አስረድተዋል።

‎አቶ በረከት አክለውም፤ ከአዲሱ የገቢ ግብር አሰባሰብ ጋር በተያያዘ በግብር አከፋፈል ላይ የሚስተዋሉ የግንዛቤ ክፍተቶችን ለመቅረፍ መስሪያ ቤቱ የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶችን እየሰጠ እንደሆነም ጠቁመዋል።

‎የግብር ስወራን ለመከላከልና ተገቢዉን ግብር በወቅቱ ባልከፈሉት ግብር ከፋዮች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሆነም አስታውቀዋል።

‎የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማሳለጥ ሁሉንም የገቢ ግብር ርዕሶችን አሟጦ በመጠቀም የገቢ መጠንን በማሳደግ ረገድ ሰፊ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል።

‎በተቋሙና በግብር ከፋዩ ዘንድ የበለጠ ቅንጅታዊ አሰራርን ለመዘርጋት እየተሰራ እንደሆነም አቶ በረከት ገልጸዋል።

‎ዘጋቢ፡ ስምረት አስማማው – ከአርባምንጭ ጣቢያችን