ባለፉት ጊዜያት ከህዝብ ለተነሱ ጥያቄዎች መንግስት ምላሽ እየሰጠ መቆየቱ ተገለጸ

ባለፉት ጊዜያት ከህዝብ ለተነሱ ጥያቄዎች መንግስት ምላሽ እየሰጠ መቆየቱ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ታኅሣሥ 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ባለፉት ጊዜያት ከህዝብ ለተነሱ ጥያቄዎች መንግስት ምላሽ እየሰጠ መቆየቱን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን ገለጹ፡፡

አቶ ፍቅሬ ይህን የገለጹት “የጉባ ብስራቶች፣ የመደመር መንግስት ትሩፋቶች” በሚል መሪ ቃል ከቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ጋር እየተካሄደ በሚገኘው ሀገራዊ የውይይት መድረክ ላይ ነው፡፡

በብልጽግና ፓርቲ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን ባለፉት ጊዜያት ከህዝብ ጋር በተደረጉ ውይይቶች የተነሱ ዋና ዋና ጉዳዮችና የተሰጡ ምላሾችን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በዚህም የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ የሰንበት ገበያዎችን ከማቋቋም ባለፈ ህገ-ወጥ ንግዶችን የመከላከል ሥራ መሠራቱን ተናግረዋል፡፡

የህዝብ ጥያቄ ከሆኑት መካከል የሺሺንዳ ቴፒ እና የዲሪ ማሻ የአስፋልት መንገድ ግንባታዎች ወደሥራ መግባታቸውን ነው የገለጹት፡፡

የቦንጋ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ ሥራ እየተሰራ ይገኛል ያሉት አቶ ፍቅሬ ፤ የቦንጋ አየር ማረፊያ ሥራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡

የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶችን የማስፋፋት ሥራም ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸው ፤ የተማሪዎች ምገባ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡

በቦንጋ ከተማ የተጀመረው የአዳሪ ትምህርት ቤት ግንባታ በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡

በተለያዩ ወረዳዎች የጤና ተቋማትን የማስፋፋት ሥራዎች መንግስት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ከሚሠራቸው ሥራዎች መካከል እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡

በክልሉ ለሰው-ተኮር ሥራዎች ትኩረት ሰጥቷል ያሉት አቶ ፍቅሬ ፤ የአቅመ-ደካሞችን ቤት የመገንባትና የመጠገን ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ዳንኤል መኩሪያ – ከቦንጋ ጣቢያችን