“መንግስት ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ በመሥራቱ ስኬቶች ተመዝግበዋል” – ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር)

“መንግስት ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ በመሥራቱ ስኬቶች ተመዝግበዋል” – ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር)

ሀዋሳ፡ ታኅሣሥ 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) መንግስት ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ በመሥራቱ ስኬቶች ተመዝግቧል ሲሉ በኢፌዴሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

“የጉባ ብስራቶች፣ የመደመር መንግስት ትሩፋቶች” በሚል መሪ ቃል ከቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ጋር ሀገራዊ ውይይት እየተካሄደ ነው፡፡

በውይይቱ የተገኙት በኢፌዴሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር) ፤ መንግስት የህዝብ ጥያቄዎችን በማዳመጥ ምላሽ እየሰጠ ይገኛል ብለዋል፡፡

በሁሉም መስኮች ውጤት የተመዘገበው መንግስት ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ መሥራት በመቻሉ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

መደረኩ ባለፉት ዓመታት የተሰሩ ሥራዎችና በቀጣይ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የጋራ ተግባቦት የሚፈጠርበት ነው ብለዋል፡፡

ክልሉ በተፈጥሮ ሃብቶች ከበለጸጉ አከባቢዎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ፤ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት የሆኑ ሰዎች መኖሪያም እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ ዞኑ የመደመር መንግስት ያስቀመጣቸውን አቅጣጫዎች በመከተል በርካታ የልማት ሥራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡

ሀገራዊ የልማት አጀንዳዎችን ይደግፋል ያሉት አቶ እንዳሻው ፤ የባህር በር ለማግኘት የተጀመረውን ሥራ የካፋ ዞን ህዝብ እንደሚደግፈው ገልጸዋል፡፡

በግብርና፣ በመንገድ፣ በከተማ ልማትና በንግድና ኢንቨስትመንት የሚሰሩ ሥራዎች ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

ካፋ ዞን በርካታ የተፈጥሮ ሀብቶች ባለቤት መሆኑን ጠቁመው ፤ ሀብቶቹን የቱሪስት መስህብ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በዞኑ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ነው የተናገሩት፡፡

ዘጋቢ፡ ዳንኤል መኩሪያ – ከቦንጋ ጣቢያችን