የፖሊዮ ክትባት ዘመቻን በተመለከተ ለጤና ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ

ሀዋሳ፡ ታህሳስ 01/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻን በተመለከተ ለጤና ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ።

‎በስልጠናው የመክፈቻ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በቡርጂ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ኡሜ ቸኮል፥ ስልጠናው ቀጣይ ለምንሠራቸው ሥራዎች አቅም የሚፈጥር በመሆኑ በአግባቡ እንዲከታተሉ አሳስበዋል።

‎ከታህሳስ 03-06/2018 ዓ.ም ድረስ ቤት ለቤት በሚደረግ ጉብኝት እድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች ለሆኑ ህጻናት እንደሚሰጥ የቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ላኦ ኮኖ ገልጸዋል።

‎ዘመቻው በዞኑ በሁሉም ቀበሌያት እንደሚሰጥ የገለጹት አቶ ላኦ ከአስራ ሰባት ሺህ በላይ ህጻናትን ለመከተብ ዝግጅት ማድረጋቸውንም ገልጸዋል።

‎ከዘመቻው ጎን ለጎን በምግብ ዕጥረት የተጎዱ ህጻናት ልየታ፣ የፊስቱላ ልየታ፣ የማርበርግ ቅኝት እና አሰሳ ህክምናዎች እንደሚደረጉ ኃላፊው ጠቁመዋል።

‎በቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ የህብረተሰብ ጤና አደጋ ቁጥጥር ቡድን መሪ አቶ ወንድሙ ሰለሞን በበኩላቸው፣ ስለ ፖሊዮ ክትባት ጠቀሜታ ግንዛቤ የመፍጠር እና ህብረተሰቡን የማንቃት ሥራ እንደሚሠራ አንስተዋል።

‎የፖሊዮ ቫይረስ ራሱን እየቀያየረ ጉዳት እያስከተለ መሆኑን ያነሱት አቶ ወንድሙ ያንን ለመከላከል በዚህኛው ዙር የሚሰጠው ክትባት ከወትሮው እንደሚለይ ገልጸዋል።

‎4ኛ ዙር የክትባት ዘመቻው ከታህሳስ 03-06/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት እንደሚሰጥ ተገልጿል።

‎ዘጋቢ: አሀዱ አሸናፊ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን