ሀዋሳ፡ ታህሳስ 01/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻን በተመለከተ ለጤና ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ።
በስልጠናው የመክፈቻ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በቡርጂ ዞን የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ኡሜ ቸኮል፥ ስልጠናው ቀጣይ ለምንሠራቸው ሥራዎች አቅም የሚፈጥር በመሆኑ በአግባቡ እንዲከታተሉ አሳስበዋል።
ከታህሳስ 03-06/2018 ዓ.ም ድረስ ቤት ለቤት በሚደረግ ጉብኝት እድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች ለሆኑ ህጻናት እንደሚሰጥ የቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ላኦ ኮኖ ገልጸዋል።
ዘመቻው በዞኑ በሁሉም ቀበሌያት እንደሚሰጥ የገለጹት አቶ ላኦ ከአስራ ሰባት ሺህ በላይ ህጻናትን ለመከተብ ዝግጅት ማድረጋቸውንም ገልጸዋል።
ከዘመቻው ጎን ለጎን በምግብ ዕጥረት የተጎዱ ህጻናት ልየታ፣ የፊስቱላ ልየታ፣ የማርበርግ ቅኝት እና አሰሳ ህክምናዎች እንደሚደረጉ ኃላፊው ጠቁመዋል።
በቡርጂ ዞን ጤና መምሪያ የህብረተሰብ ጤና አደጋ ቁጥጥር ቡድን መሪ አቶ ወንድሙ ሰለሞን በበኩላቸው፣ ስለ ፖሊዮ ክትባት ጠቀሜታ ግንዛቤ የመፍጠር እና ህብረተሰቡን የማንቃት ሥራ እንደሚሠራ አንስተዋል።
የፖሊዮ ቫይረስ ራሱን እየቀያየረ ጉዳት እያስከተለ መሆኑን ያነሱት አቶ ወንድሙ ያንን ለመከላከል በዚህኛው ዙር የሚሰጠው ክትባት ከወትሮው እንደሚለይ ገልጸዋል።
4ኛ ዙር የክትባት ዘመቻው ከታህሳስ 03-06/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት እንደሚሰጥ ተገልጿል።
ዘጋቢ: አሀዱ አሸናፊ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የደረሱ ሰብሎችን የቤተሰብ ጉልበትና የልማት ቡድን አደረጃጀት በመጠቀም በመሰብሰብ ላይ መሆናቸውን በጠምባሮ ልዩ ወረዳ የባዳ ቀበሌ አርሶ አደሮች ተናገሩ
በመጽናቴ ያገኘሁት ውጤት ነው – አርሶ አደር ደፋር ታደመ
20ኛዉ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በሰላም መጠናቀቁ ተገለፀ