የተከሰተውን ማርበርግ ቫይረስ በተቀናጀ መልኩ ፈጣን ግምገማና ምላሽ በመስጠት ለመቆጣጠር ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል – አቶ እንዳሻው ሽብሩ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 29/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የተከሰተውን ማርበርግ ቫይረስ በተቀናጀ መልኩ ፈጣን ግምገማና ምላሽ በመስጠት ለመቆጣጠር ልዩ ትኩረት መስጠቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ እና የቀውስ ክስተት አስተዳደር ሰብሳቢ አቶ እንዳሻው ሽብሩ ገለፁ፡፡
ቫይረሱ ከተከሰተ ጊዜ ጀምሮ የፌደራል ጤና ሚኒስቴርን ጨምሮ በተዋረድ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት፣ የመንግስት የልማት አጋር አካላት፣ ከቀይ መስቀል እና ከዓለም ጤና ድርጅት የተውጣጡ አካላት ያሉበት የቀውስ ክስተት አስተዳደር ተቋቁሞ በሽታውን የመከላከልና የመቆጣጠር ተግባሩ በልዩ ሁኔታ እየተመራ እንደሚገኝ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ እና የቀውስ ክስተት አስተዳደር ሰብሳቢ አቶ እንዳሻው ሽብሩ አብራርተዋል።
በተመሳሳይ ህክምናውን የሚያስተባብሩና የሚመሩ፣ የሎጀስቲክስ፣ ቅደመ መከላከያ ቡድንና ሌሎችም ተዋቅረው በየዘርፋቸው ቫይረሱን ለመቆጣጠር በሚደረገው ርብርብ ትልቅ ሥራ እያከናወኑ እንደሚገኙ አቶ እንዳሻው ገልፀዋል።
በዚህ ሂደት የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ትክክለኛና ተአማኒ መረጃዎችን ለህዝቡ በማድረስ በመከላከሉና በቁጥጥር ሥራው ትልቅ ሚና እየተወጣ በመሆኑ በቢሮው ስም አመስግነዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ አጉኔ አሾሌ በበኩላቸው፤ በአሁን ወቅት የበሽታው ቅኝት ሥራ፣ ልየታ እና የተቀናጀ ምላሽ ሥራው በስኬት እየቀጠለ መሆኑን አስረድተዋል።
የቀውስ ክስተት አስተዳደር ግብረ ሀይል ትልቅ ኃላፊነት ወስዶ እየመራ ስለመሆኑም አቶ አጉኔ ተናግረው፤ በሁሉም ዘርፍ የቫይረሱ ቁጥጥር ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው ብለዋል።
ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
3ኛው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የክለቦች ሻምፒዮና የምድብ ድልድል ይፋ ሆነ
በተሰማሩበት የስራ ዘርፍ ተገቢውን ትኩረት መስጠትና ተግቶ በመስራት ከድህነት መውጣት ይገባል – ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
ኢትዮጵያን ለዘመናት ከቆየችበት ቁስል ለማላቀቅ ባለፉት የለውጥ አመታት በርካታ ፖለቲካዊ ተግባራት ማከናወኑን መቻሉ ተገለጸ