ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉ የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 22/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ የንግድ ተቋማት ላይ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተመላከተ፡፡
ለመንግስት ሰራተኞች የተደረገውን የደመወዝ ማሻሻያ ምክንያት በማድረግ ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ የንግድ ተቋማት ላይ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የሳውላ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ።
የደመወዝ ማሻሻያን ምክንያት በማድረግ ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ 23 የንግድ ተቋማት ላይ የማሸግና አስተዳደራዊ የቅጣት እርምጃዎች መወሰዱን የሳውላ ከተማ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ጽህፈት ቤት አስታወቀ ።
ካነጋገርናቸው የመንግስት ሰራተኞች መካከል አቶ ሙልጌታ እውነቱ በቅርቡ ለመንግስት ሰራተኞች የተደረገውን የደመወዝ ማሻሻያ ምክንያት በማድረግ ምግብና ምግብ ነክ ነገሮች እና በፍጆታ ዕቃዎች ሰፊ ጭማሪ መኖሩን አንስተው የቁጥጥርና የክትትል አግባብነት ላይ ልዩነት ስለሚታይ በጥልቀት መስራት ይገባል ብለዋል።
ከንግዱ ማህበረሰብ መካከል አቶ ተስፋዬ ገብሬ እና አቶ ታደለ ሺታ በጋራ እንደተናገሩት መንግስት የሠራተኞችን ችግር በመረዳትና ኑሯቸውን ከወቅቱ ጋር ለማጣጣም የደመወዝ ማሻሻያ ማድረጉ ትክከለኛ መሆኑን አንስተው ነገር ግን አንዳንድ ስግብግብ ነጋዴዎች ከፍጆታ ዕቃዎች ላይ አላስፈላጊ ዋጋ የሚጨምሩት መበራከታቸውን ተናግረዋል።
የንግዱ ማህበረሰብ ቤተሰቡንና ህብረተሰቡን የሚያገለግል አገልጋይ መሆኑን ጠቁመው መንግስት አላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉት ላይ እየወሰደ ያለው እርምጃ መጠናከር እንዳለበትም አሳስበዋል።
የሳውላ ከተማ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ታደለ ሰለሞን እንደገለፁት ዋጋ ጭማሪ ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ያለውና ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ መኖሩን ጠቁመው የደመወዝ ማሻሻያውን ምክንያት በማድረግ የሚደረግ ጭማሪ ህገወጥ መሆኑን አስረድተዋል።
ህገወጥ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ 23 የንግድ ተቋማት ላይ የማሸግና አስተዳደራዊ የቅጣት እርምጃዎች መወሰዱን አብራርተው የነጋዴዉ ማህበረሰብ የዋጋ ዝርዝር በመለጠፍና በደረሰኝ መሸጥና፣ ህብረተሰቡም በተለጠፈው ዋጋ መሰረት መሸመትና ደረሰኝ በመቀበል ከአላስፈላጊ ወጪ ራሱን እንዲጠብቁ ጥሪ አቅርበዋል።
ዘጋቢ: ኢያሱ አዲሱ – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ፋይናንስ ቢሮ ከፌደራል ገንዘብ ሚኒስቴር እና ከክልሉ አመራር አካዳሚ ጋር በመተባበር በመንግስት ፋይናንስ አስተዳደር ዙሪያ ለኦዲት ባለሙያዎች ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል
የ20ኛዉ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን ክልላዊ የማጠቃለያ ፕሮግራም በሳጃ ከተማ እደተካሄደ ነዉ
ከ120 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው በድርያ ባለ ስድስት ወለል ሁለገብ ህንፃ ተመረቀ