በቡና ምርት አሰባሰብ ወቅት የሚኖረውን ከፍተኛ የህዝብ እንቅስቃሴ ተከትሎ የመንገድ ትራፊክ አደጋ ሆነ ሌሎች ጥፋቶች እንዳይጨምሩ በቅንጅት መሥራት እንደሚያስፈልግ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 16/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በቡና ምርት አሰባሰብ ወቅት የሚኖረውን ከፍተኛ የህዝብ እንቅስቃሴ ተከትሎ የመንገድ ትራፊክ አደጋ ሆነ ሌሎች ጥፋቶች እንዳይጨምሩ በቅንጅት መሥራት እንደሚያስፈልግ የጌዴኦ ዞን ፖሊስ መምሪያ ገለጸ፡፡
በቡና ምርት አሰባሰብ ወቅት ከወትሮ በተለየ በሚጨምረው የህዝብ እንቅስቃሴ የመንገድ ትራፊክ አደጋን ጨምሮ ሌሎች ጥፋቶች እንዳይበራከቱ በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጌዴኦ ዞን ፖሊስ መምሪያ አስታውቋል።
የጌዴኦ ዞን ፖሊስ ማህበረሰብ አቀፍ ወንጀል መከላከል ዲቪዥን ኃላፊ ምክትል ኢንስፔክተር ታምራት ምትኩ ለደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ጣቢያ በሰጡት አስተያየት፥ በአከባቢው በስፋት የሚመረተው የቡና ምርት ደርሶ የሚሰበሰብበት ወቅት በመሆኑ ከገጠር ወደ ከተማና ከከተማ ወደ ገጠር ከፍተኛ የህዝብ እንቅስቃሴዎች እንደሚደረጉ ተመላክቷል፡፡
በተለያዩ የትራንስፖርት አማራጮች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በተገቢው ጥንቃቄ ካልታጀቡ ለመንገድ ትራፊክ አደጋ መከሰት ምክንያት ይሆናሉ ያሉት ኃላፊው፥ ከህብረተሰቡና ሌሎች ባለድርሻዎች ጋር በመቀናጀት የቅድመ መከላከል ሥራዎች እየተሠሩ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በየቤተ እምነቶችና ህዝብ በሚበዛባቸው ሥፍራዎች ላይ ግንዛቤ የማስጨበጥ፣ የትራንስፖርት ፍሰትን የመቆጣጠርና የእርምት እርምጃዎችን የመውሰዱ ተግባር ተጠቃሽ መሆኑን ኢንስፔክተር ታምራት አስታውቀዋል፡፡
በሌላ በኩል በቡና ሥርቆት ወንጀል በመሰማራት ህብረተሰቡን በሚያማርሩ አካላት ላይ ህበረሰቡን ባሳተፈ መልኩ የመለየትና አስተማሪ እርምጃ የመውሰዱ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠሉን የገለጹት ኃላፊው ወቅቱ ከፍተኛ የገንዘብ ልውውጥ የሚካሄድበት በመሆኑ ሀሰተኛ የገንዘብ ኖት ዝውውርን የመቆጣጠር ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ህብረተሰቡ ከመንግስት ጎን በመሆን ወንጀልን ከመከላከል ሥራ ጎን ለጎን የአከባቢውን ሁለንተናዊ ሰላም በመጠበቅ የበኩሉን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡
ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
ለትምህርት ሥራ ስኬታማነት ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነትና በጋራ መስራት እንዳለባቸው ተገለፀ
በበጀት አመቱ በ71 ሺህ 219 መዛግብት ላይ ውሳኔ መስጠት መቻሉ ተገለጸ
የጉራጌ ማህበረሰብ ባህላዊ እሴቶች ሳይበረዙ ለትውልድ ለማስተላለፍ የኪነ ጥበብ ዘርፉን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝ የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ