ለ20ኛ ጊዜ “ዲሞክራሲያዊ አንድነት፤ ለሀገራዊ መግባባት” በሚል መሪ ቃል የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል ለማክበር የጋሞ ዞን ም/ቤት የዝግጅት ሥልጠና እየሰጠ ነው
በዘንድሮው ዓመት ለ20ኛ ጊዜ “ዲሞክራሲያዊ አንድነት፤ ለሀገራዊ መግባባት” በሚል መሪ ቃል በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆሳዕና ከተማ የሚከበረውን የብሔር፣ ብሔሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓልን አስመልክቶ፣ በጋሞ ዞን እስከታችኛው መዋቅር የሚተገበር የዕቅድ አፈጻጸም ዙሪያ የአሰልጣኞች ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል ።
የጋሞ ዞን ህዝብ ምክር ቤት ም/አፈ- ጉባኤ ወ/ሮ አብዮት አባይነህ እንደገለጹት፣ ሥልጠናው በየደረጃው በህገ መንግስቱ ላይ የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር የእርስ በርስ ትስስርን የሚያጎለብት ፣ህብረብሔራዊ አንድነትን የሚያጠናክርና ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠር የሚያግዝ ነው።
የጋሞ ዞን የአስተዳደር ተወካይ እና የኢንቨስትመንት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደረጀ ጳውሎስ እንዳሉት ፣ 19ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን አርባ ምንጭ ላይ መከበሩ አርባ ምንጭና አከባቢውን በስፋት ያስተዋወቀ በድምቀቱም ከፍተኛ የሆነና ለሌሎችም ማሳያ የሆነ እንደነበረ ነው የገለጹት።
ዛሬ እየተሰጠ የሚገኘው ስልጠና የጋሞ ዞን ህዝቦች የብዝኃነት እሴቶችን በማጠናከር፣ ሀገራዊ መግባባትን በሚያጎለብት መልኩ በዓሉን በስኬት ለማክበር እየተደረገ ያለውን ጥረት ያመለክታልም ብለዋል።
ዘጋቢ ፡ አዕላፍ አዳሙ፦ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
ለግብርናው እድገት መንግስት ከሚያደርገው ጥረት ጎን ለጎን የግብርና አጋር አካላት ድጋፍ የማይተካ ሚና እንዳለው የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ ገለጸ
በዳውሮ ዞን ታርጫ ከተማ የጥምቀት በዓል በተለያዩ ሀይማኖታዊ ክዋኔዎች በድምቀት ተከብሯል
የ1447ኛው ዓመተ ሂጅራ የሀጅ ምዝገባ ጥር 18 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ የሲዳማ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አስታወቀ