ኑሮአቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ሴቶችንና ሕፃናትን ሁሉም የአቅሙን በመደገፍ የበኩሉን እንዲወጣ የዲላ ከተማ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ጥሪ አቀረበ

‎መምሪያው የዓመቱን የነጭ ሪቫን የሴቶች ቀንና ዓለም አቀፍ የሕጻናት ቀን አስመልክቶ የፓናል ውይይት አካህዷል፡፡

‎የዲላ ከተማ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ዜና ክፍሌ እንደገለፁት ከሴቶች አደረጃጀት፣ ከፍትህ ተቋማትና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት በመስጠት በሕፃናትና በሴቶች ላይ የሚደርሱ ፆታዊ፣ ስነ ልቦናዊና ማህበራዊ ጥቃቶችን ቀድሞ ለመከላከል እየሠሩ ነው፡፡

‎በሴቶችና ሕፃናት ላይ የተለያዩ አካላት በደል ሲያደርስባቸው ከህግ ባለሙያዎች ጋር በመሆን ፍትህ እንዲያገኙ በማድረግ በጥፋተኛውም ህጉ በሚደነግገው መሰረት የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ ማድረጋቸውንም ወ/ሮ ዜና አስታውሰዋል፡፡

‎ኑሮአቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ሴቶችና ሕፃናት ለጥቃት ተጋላጭ ስለሆኑ ሁሉም የአቅሙን በመደገፍ የበኩሉን እንዲወጣ ኃላፊዋ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

‎በውይይቱ ከተሳተፉት ተማሪዎች መካከል ከፍያለው አየለና መክሊት ፀጋዬ በተለያዩ ጊዜያት ባገኙት ግንዛቤ በየትምህርት ቤታቸው ባሉ የሚኒ ሚዲያና ሕዝብ በሚሰበሰብበት ለተማሪዎችና ለማህበረሰቡ ትምህርት በመስጠት በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ቀድሞ ለመከላከል የድርሻቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

‎በየአካባቢው በሴቶችም ሆነ በሕፃናት ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በመከላከል ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ተማሪዎቹ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

‎በውይይቱ መጨረሻም ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ሴቶች በከተማ አስተዳደሩ ካሉት መዋቅሮች በመለየት የአልባሳትና ንጽህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

‎ዘጋቢ: ውብሸት ኃ/ማርያም – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን