በከተማው ንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቂ ባለመሆኑ መቸገራቸውን በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ
የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ውሃ አገልግሎት በበኩሉ በከተማው ያለውን የውሃ ችግር ለመፍታት እየሠራ መሆኑን ገልጿል።
ወ/ሮ አበበች ሽብሩ፣ አቶ ታደለ አበበ እና ሌሎችም የከተማዋ ነዋሪዎች፥ ይርጋጨፌ ውሃማ አካባቢ እንደሆነች የሚታወቅ ቢሆንም በተለይም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ለማግኘት መቸገራቸውን ነው የሚገልጹት።
በከተማው ላይ የውሃ አቅርቦት በቂ ካለመሆኑ የተነሳ ንፁህ ያልሆነ የምንጭ ውሃ ለመጠቀም እንደሚገደዱና ለተለያዩ የውሃ ወለድ በሽታዎች እንደሚዳርጋቸውም ተናግረዋል።
የሚመለከታቸው አካላት ህብረተሰቡን በማስተባበር ንፁህ የመጠጥ ውሃ ተጠቃሚዎች እንዲያደርጓቸው በመሥራት ችግሩን እንዲፈቱ ጠይቀዋል።
የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ውሃ አገልግሎት ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤልያስ ታሪኩ፤ በከተማዋ ያለው የውሃ ሽፋን ዝቅተኛ ወይም 15 በመቶ ብቻ እንደሆነ ጠቁመው ህብረተሰቡ የሚያነሳው ቅሬታ ትክክል እንደሆነ ገልጸዋል።
ከጊዜ ወደጊዜ የህዝብ ቁጥር መጨመር፣ ከአገልግሎት ብዛት የተነሳ የውሃ ፓምፖች ብልሽት፣ የመብራት መቆራረጥና ኃይል ማነስ በዋናነት በከተማዋ ላለው የውሃ ችግር በምክንያትነት አንስተዋል።
ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር እየሠሩ እንዳሉ በመግለፅ ህብረተሰቡም የድርሻውን መወጣትና ማገዝ አለበት ብለዋል።
ዘጋቢ: ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
በኩታ ገጠም እርሻ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች የአርሶአደሩን ኑሮ ለማሻሻል አይነተኛ ሚና እንዳለው ተገለጸ
የእምነት ተቋማት ለአገረ መንግስት ግንባታ ቁልፍ ሚና ያላቸው በመሆኑ ለሀገር ብልጽግና ኃይል አድርጎ መጠቀም እንደሚገባ ተመላከተ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የኢትዮጵያ ብልፅግና እንዲረጋገጥ አዎንታዊ አስተዋጽኦ ማበርከቷ ተገለጸ