የወጣቶች መዝናኛ ማዕከላት ወደ ስብዕና ማቀልፀጊያነት እንዲሻገሩ በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ ተገለጸ

የወጣቶች መዝናኛ ማዕከላት ወደ ስብዕና ማበልፀጊያነት እንዲሻገሩ በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ሕዳር 03/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የወጣቶች መዝናኛ ማዕከላት ከማዘወተሪያት ባለፈ ወደ ስብዕና ማበልፀጊያነት እንዲሻገሩ በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ጉዳይና በጎፈቃድ አገልግሎት ኮሚሽን አስታወቀ።

ኮሚሽኑ የአፍላ ወጣቶችና የወጣቶች አቅም ግንባታ ፕሮግራም ጋር በመተባበር በወጣቶች ስብዕና ማበልፀጊያ ማዕከላት ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር በጂንካ ከተማ መክሯል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ጉዳይና በጎ አገልግሎት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ማርቆስ ማቴዎስ ባስተላለፉት መልክት ወጣቶች ዕውቀትና ክህሎትን እንዲያገኙና ጊዜያቸውን አልባሌ ቦታ እንዳያሳልፉ ታስበው የተገነቡ የመዝናኛ ማዕከላት ከማዘወተሪያነት ባለፈ የስብዕና ማዕከል እንዲሆኑ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።

ከ537 በላይ የስብዕና ማዕከላት በክልሉ መኖሩን ያስረዱት ኮሚሽነር አቶ ማርቆስ÷ ሁሉም ማዕከላት 16 የተለያዩ አገልግሎቶችን መስጠት የሚችል ሞዴል ማዕከል እንዲሆኑ እየተሠራ መሆኑን ገልፀው የመድረኩ የትኩረት አቅጣጫዎችን አብራርተዋል።

ወጣቱ በአከባቢው ልማት በንቃት በመሳተፍ ተጠቃሚነቱን እንዲያረጋግጥ የሚከናወኑ የስብዕና ማበልፀጊያ ማዕከላት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የድርሻቸውን እንደሚወጡ የውይይቱ ተሳታፊዎች ገልፀዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን