የሐይማኖት ተቋማት በአገር አንድነት፣ ሰላም ማስፈንና ግጭት አፈታት ሂደት ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 03/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሐይማኖት ተቋማት በአገር አንድነት፣ ሰላም ማስፈንና ግጭት አፈታት ሂደት ወሳኝ ሚና እንዳላቸው የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ደምሴ አድማሱ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡
ዋና አስተዳዳሪው ግጭትን በሰላም ወደሚፈታባት እና የብሔር ብሔረሰቦች መገኛ ወደሆነችው ለምለሚቷ ከተማ እንኳን ደህና መጣችሁ ብለዋል።
ደምሴ አድማሱ (ዶ/ር)፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ በአንድነት የምትታወቅ ሲሆን ይህንን አንድነት በማጠናከር ረገድ የሃይማኖት ተቋማት ወሳኝ ሚና አላቸው ብለዋል።
የሰው ልጅ ለሰላም ፍለጋ ወደ ፈጣሪና ወደ ሃይማኖት ተቋማት የሚመለከት በመሆኑ አመጽና ክፋትን ለመዋጋትም ጭምር ተቋማቱ ከፍተኛ ድርሻ እንደሚጫወቱ አጽንኦት ሰጥተዋል።
አክለውም፤ በክልላቸውና በአገሪቷ በዘላቂነት መለወጥ የሚቻለው ሰላም ሲኖር ብቻ መሆኑን በመጥቀስ ማህበራዊ ትስስርንና ሀገረ መንግሥትን በሰላም ግንባታ ለማጠናከር የሃይማኖት ተቋማት ሚና እጅግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
የጋሞ ዞን አስተዳደር የሃይማኖት ተቋማት ተቻችለውና ለሰላም ዘብ መቆም እንዲችሉ ያልተቋረጠ ድጋፍ እንደሚያደርግ ቃል ገብተዋል።
የአርባ ምንጭ ከተማ ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር)፤ የሰላምን አስፈላጊነት እና ከተማዋ ለሰላም እያደረገች ያለችውን ጥረት አብራርተው ጉባኤውን ለማስተናገድ ዕድል በማግኘታቸው እንደተደሰቱ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በአንድነቷ የምትታወቅ ብትሆንም “በክፉ ሀሳብ በቆሙት” በመፈተን ላይ እንደቆየች እና ሀገሪቱ ያለውን አቅም እንዳትጠቀም መደረጓን አስታውሰዋል፤ ቀደምት አባቶች እንቅፋቶችን እንዳለፉ ሁሉ ዛሬም ትውልዱ የሰላም ችግሮችን የመፍታት ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል።
በሰላም እጦት ምክንያት በሀገሪቱ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እንደደረሱ አመልክተዋል።
ሆኖም ከተማዋ ሁለንተናዊ የሰላም ንፋስ እንዲነፍስ እያደረገች እንደምትገኝ እና አመርቂ ውጤትም በማስመዝገብ ላይ እንዳለች አብራርተዋል።
አርባ ምንጭ “በእርጥብ ሳር ጠብን ያበረዱበት ስፍራ” መሆኗን በመጥቀስ የሰላም ምልክት መሆኗን ተናግረዋል።
የክልሉን ህዝብ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሰላም ወሳኝ በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል።
ይህ 5ኛው ሀገር አቀፍ ጉባኤ ተቀራርቦ ስለሰላም አብሮ ለመስራት እንዲሁም የሀገሪቱን ቱባ ባህሎችና ህብረብሔራዊነትን ለማጎልበት ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው አጽንኦት ሰጥተዋል።
በመሆኑም ወደ ከተማዋ የመጡ እንግዶች የከተማዋን ተስፋ ሰጪ ልማትና ተፈጥሮ ሀብቶች እንዲሁም ድንቅ ባህሏን እንዲመለከቱና ሰላማዊ ቆይታ እንዲያደርጉ ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ አማሮ አርሳባ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በግሉ የኢንቨስትመንት ልማት ዘርፍ እየታዬ ያለውን መነቃቃት ይበልጥ ለማጎልበት ከመንግስት በኩል የሚጠበቁ ድጋፎች መጠናከር እንዳለባቸው የደቡብ ኦሞ ዞን ምክር ቤት አሳሰበ
የትራፊክ አደጋን መከላከል የማህበረሰቡ የሁል ጊዜ ተግባር መሆን እንደሚገባ ተገለፀ
በሴቶች ላይ የጡትና የማህፀን በር ካንሰር የሚያስከትለውን ሞት ለመቀነስ የካንሰር ቅድመ ምርመራ መደረግና ህክምና መውሰድ ወሳኝ መሆኑ ተጠቆመ