በሴቶችና ህጻናት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለመቀነስ የቅድመ መከላከል ሥራዎች ላይ ማተኮር እንደሚገባ ተገለጸ
በሴቶችና ህጻናት ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ለመቀነስ የቅድመ መከላከል ሥራዎች ላይ ማተኮር እንደሚገባ የጌዴኦ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት አስታውቋል።
የዞኑ ፍርድ ቤቶች በ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸምና በሚቀጥሉ አምስት ዓመታት መሪ ዕቅዶች ዙሪያ የባለድርሻ አካላት መድረክ በይርጋጨፌ ከተማ አካሂዷል፡፡
በመድረኩ የጌዴኦ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ሳሙኤል በፍቃዱ፤ በ2017 በጀት ዓመት የዞኑ አስተዳደር ከፍትህ ተቋማት ጋር በመቀናጀት በቡና እና ሌሎች ምርቶች ላይ የሚሰተዋሉ የስርቆት ወንጀሎችን ለመከላከል ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል፡፡
በሀገር ብሎም በክልል ደረጃ የተጀመረውን የፍትህ ዘርፍ ትራንስፎርሜሸን ተግባራዊ የማድረጉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የጠቆሙት ፕሬዝዳንቱ፤ ቅሬታ የተነሳባቸውን ዳኞች በጊዜያዊነት ከሥራቸው በማገድ የማጣራት ሥራዎች እየተካሄዱ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሴቶችና ህጻናት የሚደርሱ መጠነ ሰፊ የወንጀል ድርጊቶች መስተዋላቸውን የጠቆሙት አቶ ሳሙኤል፤ ችግሮችን ለመቀነስ ወንጀለኞች ላይ ከሚወሰደው የእርምት እርምጃ በተጨማሪ በቅድመ መከላከል ሥራዎች ላይ በስፋት መንቀሳቀስ ተገቢ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ምስጋና ዋቃዮ በበኩላቸው፤ መንግስት ፍትህ እንዳይዛባ ለአቅመ ደካሞች ነጻ የጥብቅና አገልግሎት በመስጠት ፍትህን ለማስፈን ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ቢሆንም በዞኑ በ2017 በጀት ዓመት ሴቶችና ህጻናት አረጋዊያንና አቅመ ደካሞችን የፍትህ ጥያቄ ከመመለስ አኳያ ክፍተቶች መስተዋላቸውን አንስተዋል፡፡
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የነበሩ ጉድለቶችን ለማረም ከባለድርሻ አካላት ጋር ተቀናጅተው መሥራት እንደሚገባ የገለጹት አፈ ጉባኤዋ፤ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መቅረፍ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፍትህ ትራንስፎርሜሽን ውጤታማ ለማድረግ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡
ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
በሴቶችና ህጻናት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለመቀነስ የቅድመ መከላከል ሥራዎች ላይ ማተኮር እንደሚገባ ተገለጸ

More Stories
አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ሳውላ ካምፓስ ለ9ኛ ጊዜ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን 121 ተማሪዎችን አስመረቀ
ዲግሪው “ወረቀት ብቻ ሳይሆን፣ የሀገር ተስፋና የትውልድ ኃላፊነት ነው” – አፈወርቅ ካሱ (ፕ/ር)
በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ዶ/ር አስፋው ዲንጋሞ ገለጹ