ለሆስፒታሉ የተበረከቱ የህክምና ቁሳቁሶች ለአገልግሎት ጥራት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ የቦንጋ ገብረጻድቅ ሻዎ አጠቃላይ ሆስፒታል ባለሙያዎች ተናገሩ

“ሂውማን ብሪጅ ኢትዮጵያ” ከተሰኘ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት የ150 ሚሊየን ብር ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የህክምና ቁሳቁሶችን ለሆስፒታሉ ያበረከተ ሲሆን የህብረተሰቡን የጤና ችግር እንደሚያሻሽሉ ሆስፒታሉ ገልጿል።

የቁሳቁሶቹ መገኘት በማህበረሰቡ ጤና እና በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚኖረውን ፋይዳ በተመለከተ የቦንጋ ገብረጻድቅ ሻዎ አጠቃላይ ሆስፒታል ባለሙያዎች አስተያየት ሰጥተዋል።

የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር ዋስይሁን መስፍን ባለሙያዎች ከታማሚው ከሚያገኙት መረጃ ባሻገር ቁሳቁሶች የሚሰጡት ውጤት መሠረታዊ ነው ብለዋል።

በሆስፒታሉ የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስትና የህሙማን ክፍል አስተባባሪ ዶክተር ሽመልስ አሪቶ፤ የህክምና መሳሪያዎቹ መገኘት የታካሚዎችን እንግልት የሚቀንስና የባለሙያዎችን ተነሳሽነት የሚያሳድግ ነው ብለዋል።

የቦንጋ ገብረጻድቅ ሻዎ አጠቃላይ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ ፍቅረማርያም ጳውሎስ በበኩላቸው፤ ሆስፒታሉ እቃዎቹን ለመግዛት አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ በነበረበት ወቅት የተገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ዘመናዊ እቃዎቹ የአገልግሎት አሰጣጡን የሚያቀላጥፉና የህብረተሰቡን የጤና ችግር የሚያሻሽሉ ናቸው ብለዋል።

ዘመናዊና በኤክትሮንክስ ሲስተም የሚሰሩ በመሆናቸው በአጠቃቀም ወቅት ጉዳት እንዳይደርስባቸውና ብክነት እንዳያጋጥም ጥብቅ ቁጥጥር ይደረጋል ብለዋል።

ከሆስፒታሉ ተገልጋዮች መካከል ያነጋገርናቸው አቶ ሀብታሙ ኃይሌ በአካባቢው ሪፈራል ሆስፒታሎች ባለመኖራቸው ታካሚዎች ይንገላቱ እንደነበር አስታውሰው፤ ይህ ድጋፍ የጤና አገልግሎቱን እንደሚያሻሽል ተናግረዋል።

ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው የኦፕሬሽን አልጋዎች፣ የአንስቴዥያ ማሽን፣ የቀዶ ጥገና እቃዎች፣ የተለያዩ አልባሳት፣ ዊልቸሮች፣ የተኝቶ ታካሚ አልጋዎች፣ የዐይን ህክምና መሣሪያዎችና ሌሎችም ከተበረከቱ ቁሳቁሶች መካከል ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ አሳምነው አትርሳው – ከቦንጋ ጣቢያችን