የመንግሥት ሠራተኞች ሀገሪቱ ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ በመገንዘብ ብሔራዊ ጥቅሟን ለማስከበር የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገለጸ

“የታደሰ ጂኦ ስትራቴጂያዊ ቁመና በሁሉም ኢትዮጵያዊያን የጋራ ትጋት” በሚል መሪ ቃል በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ከተማ ለሚገኙ የመንግስት ሠራተኞች ስልጠና ተሰጥቷል፡፡

ከ3ሺህ በላይ የመንግስት ሠራተኞች በተሳተፉበት በዚህ የስልጠና መድረክ ሀገሪቱ ወደ ነበረችበት ገናናነት ለመመለስ ሁሉም ሠራተኛ የድርሻውን እንዲወጣ የጋራ ግንዛቤ እንዲይዝ ታስቦ የተዘጋጀ እንደሆነ የገለፁት የይርጋጨፌ ከተማ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ዳዊት የጋ ናቸው፡፡

በከተማው የሚገኙ የመንግሥት ሠራተኞች ኢትዮጵያ ያለችበት ጂኦ ስትራቴጂያዊ ቁመናን በመረዳት ብሔራዊ ጥቅሟን ለማስከበር የጋራ ግንዛቤ የተያዘበትና ስኬታማ መድረክ እንደነበረ አስረድተዋል፡፡

የኢትዮጵያን ከፍታ በሚጠሉ የውጭ ባዳዎችና የውስጥ ባንዳዎችን በመከላከል የተሰጣቸውን ተግባር በትጋትና በኃላፊነት እንዲፈጽሙ አቶ ዳዊት አሳስበዋል፡፡

የስልጠናው ተሳታፊዎችም ብሔራዊ ጥቅምና ጂኦ ስትራቴጂያዊ ቁመና የጠራ ስዕል የፈጠረ ስልጠና እንደሆነ ገልጸው ሃገሪቱ ከእኛ የምትፈልገውን ሁሉ ለመስጠት ቁርጠኛ ነን ብለዋል።

ዘጋቢ፡ አማኑኤል ትዕግስቱ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን