ቡናን በዘመናዊ መንገድ በማልማታቸዉ በተተከለ አንድ አመት ጊዜ ዉስጥ ማፍራት መጀመሩን በሸካ ዞን የኪ ወረዳ የአላሞ ቀበሌ ወጣት ሞደል አርሶ አደሮች ተናገሩ

የየኪ ወረዳ አስተዳደር በበኩሉ ዘንድሮ ብቻ 5 ሺ ሄክታር ያረጁ ቡናዎችን በማስጎንደል በዘመናዊ ቡና ለማስተካት አቅዶ እየሰራ መሆኑን አስታዉቋል።

በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር የቴፒ ብሄራዊ ቅመማ ቅመም ማዕከል የሰጣቸዉን ምርጥ የቡና ችግኝ በዘመናዊ አሰራር በማልማታቸዉ በተከሉ በአንድ አመት ጊዜ ዉስጥ ቡናቸዉ ምርት መስጠት መጀመሩን ነዉ በየኪ ወረዳ አላሞ ቀበሌ ሞደል ወጣት አርሶ አደር ይንገስ ጌታቸዉና ብርሃኑ ጌታቸዉ የተናገሩት።

አርሶ አደሮቹ ከዚህም በላቀ ደረጃ በጥራትና በሰፋት ቡናን በማምረት ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ እንዲችሉ አሁን ላይ ያለባቸዉን የመሬት አቅርቦች ችግር ሚመለከተዉ አካል እንዲፈታላቸዉ ጠይቀዋል።

ሁሉም አርሶ አደሮችና ሚመለከታቸዉ አካላት በሙሉ ያረጁና ምርታማነታቸው ያበቃ ቡናዎችን ምረታማነታቸዉ በመርምር ማዕከል በተረጋገጡ በመተካቱ ረገድ ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር የቴፒ ብሄራዊ ቅመማ ቅመም ማዕከል ዳይሬክተር ዶክተር ደረጀ ቱሉ አሳስበዋል።

የየኪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ተሰማ በበኩላቸዉ፤ በወረዳዉ ካለዉ ቡና ሽፋን አብዛኛዉ ያረጀ በመሆኑ ዘንድሮ ብቻ 5 ሺ ሄክታር በማስጎንደል በዘመናዊና ምርታማ ቡናዎች ለመተካት መታቀዱን ገልጸዉ፤ በተለይም በቡና ጥራት ማስጠበቅ ላይ ሁሉም ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ አሳስበዋል።

የወጣቶቹ የመሬት አቅርቦት ጥያቄ በሚፈታበትም ዙሪያ ከሚመለከታቸዉ አካላት ጋር ይሰራል ብለዋል።

ዘጋቢ: ጌትነት ገረመዉ – ከማሻ ጣቢያችን