ህሙማንን የመጠየቅና የመርዳት ባህል ሊዳብር እንደሚገባ የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል ገለፀ
የከተማው ፖሊስ በሆስፒታሉ የሚገኙ ህሙማንን በመጠየቅ የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስና ሌሎች ግብአቶችን ድጋፍ አድርጓል።
የአርባ ምንጭ ከተማ ህዝብ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ጥሩነሽ ተስፋዬ፤ የታመመን መጠየቅ፣ የተቸገረን መርዳት ከህሊና እርካታ ባለፈ በፈጣሪ ዘንድ ተወዳጅ ተግባር በመሆኑ የአብሮትና የመረዳዳት ልምዳችን ሊዳብር ይገባል ብለዋል።
የከተማው ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር ክበበው አዳል እንዳሉት፤ የፖሊስ አባላቱን በማስተባበር ከከተማው ህብረተሰብ ከተሰበሰበ ድጋፍ የመስቀል በዓልን ምክንያት በማድረግ የታመሙ ወገኖችን በመጎብኘት የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስ እና ሌሎች ግብአቶችን ማበርከት ተችሏል።
የከተማው ፖሊስ ሰላምን ከማስጠበቅ ባሻገር በሚያደርገው ማህበራዊ እንቅስቃሴ የህሊና እርካታ የሚያገኝበት በመሆኑ የሚደረጉ በጎ ተግባራትን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ኮማንደሩ አረጋግጠዋል።
የከተማው ሰላምና ፀጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ገበየሁ ፃራ የፀጥታ መዋቅሩ ጉዳት የደረሰባቸውን አባላት ሲጎበኝ መቆየቱን ገልፀው፤ ህሙማንን መጠየቅ ደግሞ በህብረተሰቡ ዘንድ አክብሮነት የሚያስገኝ ስለሆነ ሌሎች ተቋማትም ከዚህ ልምድ ሊወስዱ ይገባል ብለዋል።
የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ ዶ/ር አምባቸው ዱምአ በበኩላቸው፤ በሆስፒታሉ የሚገኙ ህሙማንን በሀይማኖት ተቋም፣ በቡድን ብሎም በግል የመጠየቅ ባህል የተለመደ ቢሆንም በተቋም ደረጃ አባላትን አስተባብሮ ለህሙማኑ ድጋፍ በመደረጉ አድናቆታቸውን ገልፀዋል።
ከምንም በላይ የህሊና እርካታ የሚሰጥ በጎ ተግባር የፈፀሙ የከተማው ፖሊስ አባላት ላበረከቱት አስተዋፅኦ በህሙማኑና በሆስፒታሉ ስም አመስግነዋል።
በሆስፒታሉ ተኝተው ህክምና የሚደረግላቸው ታካሚዎች በተደረገው ድጋፍ መደሰታቸውን ገልፀው የመጠያየቅና የመተባበር ባህላችን ሊዳብር ይገባል ብለዋል።
ዘጋቢ፡ ገነት መኮንንን – ከአርባምንጭ ጣቢያችን
ህሙማንን የመጠየቅና የመርዳት ባህል ሊዳብር እንደሚገባ የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል ገለፀ

More Stories
የተለያዩ የህክምና መድሀኒቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት መቻላቸውን በሚዛን አማን ከተማ በማህበረሰብ አቀፍ ፋርማሲ ሲገለገሉ ያገኘናቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ገለፁ
የየም ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ “ሄቦ” በዓል በደማቅ ስነ ስርዓት በሣጃ ከተማ እየተከበረ ነው
በክረምት ወራት የታየውን ትጋት በበጋውም ለመድገም ቁርጠኞች መሆናቸውን በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ከተማ ወጣቶች ተናገሩ