ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በከተማው አስተማማኝ ሰላም ማስፈኑ ተገለጸ

ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በከተማው አስተማማኝ ሰላም ማስፈኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 02/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በከተማው አስተማማኝ ሰላም ማስፈኑ የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ፀጥታ ጽ/ቤት አስታወቀ።

‎ከተማው የሚታወቅበትን የሰላም እሴት ለማስቀጠል ህዝቡን አጋዥ ሀይል አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ የገለፀው ደግሞ የከተማው ፖሊስ ነው፡፡

‎የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ከሆኑት መካከል አቶ ዳዊት ዳልጋ እና ሀምሳለቃ በቀለ ሀብቴ ሰላም ፀጥታ የጋራ ጉዳይ ነው ብለው ከተማው የሚታወቅበትን ሰላም ለማስቀጠል እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል ።

‎ሲስተር አስቴር ይዙ እና ወ/ሮ አበበች ባልቻም የከተማው ነዋሪዎች ሲሆኑ በከተማው የሚታየውን ሰላም ወደ አስተማማኝ ደረጃ እየደረሰ ይገኛል ብለዋል።

‎ኮማንደር ክበበው አዳል የአርባምንጭ ከተማ ፖሊስ አዛዥ ሲሆኑ ወንጀል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስን የሚያስከትል በመሆኑ በከተማውም ሰላምን ለማስፈን ሰፊ እና የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ይገኛል ።

‎በከተማዋ የተለያዩ ኩነቶች የሚከናወኑባት እና የቱሪስት መዳረሻ በመሆኗ ለሰላም እጦት መነሻ የሚሆኑ እንቅስቃሴዎች ሲከሰቱ ህብረተሰ በፍጥነት ለፀጥታ ሀይሉ እንደሚያሳውቅ አረጋግጠዋል።

‎ከሀገር ሽማግሌዎች፣ ሀይማኖት ተቋማት፣ ከተለያዩ አደረጃጀቶች ፣ ከአከባቢው ነዋሪዎች እና ከአጋር ድርጅቶች ጋር በጋራ በመሆን ሰፋፊ ስራዎችን በመስራት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

‎የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪ ሰላም ወዳድ እና ሰሚ ማህበረሰብ ነው ያሉት ኮማንደር ክበበው፥ ይህንን በጎ እድል ለማስጠበቅ እንሰራለን ብለዋል።

‎ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በከተማው አስተማማኝ ሰላም እንዲፈጠር ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት እየተሰራ መቆየቱን ያወሱት የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ፀጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ገበዬሁ ፃራ፥ ህብረተሰቡ ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመሆን የራሱን ሰላምና ደህንነት ለማስጠበቅ እየሰራ እንደሚገኝ አውስተው ሰላም እንዳይደፈርስ በ8 ቱ ቀበሌያት በየጊዜው ጠንካራ ውይይት እንደሚደረግ አረጋግጠዋል።

‎በተጨማሪም የፀጥታ ስራን ህዝባዊ በማድረግ አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን ስልጠናዎች እየተሰጡ ይገኛሉ በዚህም ለውጥ እየተመዘገበ ነው ብለዋል።

ዘጋቢ ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን