በሀገሪቱ የሕግ የበላይነትን የማስፈን እና ሰላም የማረጋገጥ እርምጃ የመንግስት ተቀዳሚ ተግባር ነው – የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

በሀገሪቱ የሕግ የበላይነትን የማስፈን እና ሰላም የማረጋገጥ እርምጃ የመንግስት ተቀዳሚ ተግባር ነው – የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

በሀገሪቱ የህግ የበላይነትን የማስፈን እና ሰላም የማረጋገጥ እርምጃ የመንግስት ተቀዳሚ ተግባር መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ዛሬ በሰጠው መግለጫ አስታወቀ።

ግጭት እና ጦርነት የዜጎችን ሰላም እና ደህንንት አደጋ ላይ ይጥላሉ፣ ዲሞክራሲያዊ ስርዓቱን ያውካሉ፣ ውዱን የሰው ልጅ ህይወት ይቀጥፋሉ፤ ሃብትና ንብረትንም ያወድማሉ፤ ስለሆነም የሃገራችንን ሰላም ማረጋገጥ ማሳካት የመንግስት ተቀዳሚ አላማ መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ኃላፊ ሚኒስትር ዶ/ር ለገሰ ቱሉ ገልጸዋል።

መግለጫው፣ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት እንድትሆን አፍሪካዊ የሰላም ተምሳሌት ልትሆን ይገባታል፤ ሰላም የሰፈነባት ኢትዮጵያ ዕድገቷ የተረጋገጠ ይሆናልም፤ በቀጠናው እና በአፍሪካም ተጽእኖ ፈጣሪ ትሆናለች ብለዋል።

በመሆኑም አሁን እየተረጋገጠ ያለውን አንጻራዊ ሰላም ቀጣይነቱን ማረጋገጥ አመራሩ በተለያየ ጊዜያት መክሮ አስምሮበታል ብለዋል።

የሰላም በሮቻችንን ለሁሉም ኃይሎች ክፍት ማድረጋችን በመላ ሃገሪቱ እየሰፈነ ላለው ሰላም መሰረት ሆኗል ያለው መግለጫው፣ የሰሜኑ ግጭት በተቀመጠለት አቅጣጫ በስኬታማነት እየተተገበረ እንደሚገኘም ጠቁሟል።

በመግለጫው፣ ከሸኔ ጋር የተጀመረው ሰላም የማስፈን ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የተገለጸ ሲሆን በቤንሻንጉል እና በጋምቤላ የሚገኙ ታጣቂ ኃይሎችም በተከፈተው የሰላም በር መጠቀም በመቻላቸው አካባቢዎቹ የተረጋጉ እና ሰላማቸው የተረጋገጠ መሆን ችሏል ተብሏል።

መንግስት ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን፣ የግዛት አንድነትን እና ህብረ ብሔራዊነትን ለሚያረጋግጥ ሰላም ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ አያስቀምጥም ያለው መግለጫው፣ ሰላም ለማጽናት እና ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን ከአደጋ ለመጠበቅ አንድ ሀገራዊ ጠንካራ የመከላከያ ኃይል እና የፌደራል ፖሊስ የመገንባት የተሳካ ስራም ተጠንክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።

በክልሎችም እንዲሁ የተቀናጀ ወንጀሎችን መከላከል የሚችል የተጠናከረ መደበኛ ፖሊስ የመገንባት ስራም በተሳካ መልኩ እየቀጠለ መሆኑ ተገልጿል።

በመግለጫው ሰላማችንን የማይፈልጉ ኃይሎች ዛሬም እንዳሉ የተጠቆመ ሲሆን ከውስጥ የነጠላ እውነትን በኃይል በሌሎች ላይ ገዢ ለማድረግ የሚጥሩ ኃይሎች፤ ከውጭ ደግሞ ታሪካዊ ጠላቶቻችን መሞከራቸው አልቀረም ነው የተባለው።

ስለሆነም፣ የሀገሪቱን ሰላም ለማረጋገጥ የተጀመረው ጠንካራ የጸጥታ እና የደህንነት ተቋም የመገንባት ስራም መንግስት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።

ሰላምችንን የተሻለ ለማድረግ ቂምን መሻር እና ከሂሳብ ማወራረድ እሳቤ በመውጣት የሽግግር ፍትህን ለማስፈን የተጀመረው ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ተብሏል።

ማህበረሰቡም የሰላም ማስፈኑን ሂደት እንዲደግፍ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በመግለጫው ጥሪ አቅርቧል።