በአንድ ጀምበር ከ470 ሺህ በላይ ችግኞች ይተከላሉ – ጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት
ሀዋሳ፡ ሐምሌ 22/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በአረንጓዴ አሻራ ፕሮግራም በአንድ ጀምበር ከ 470 ሺህ በላይ ችግኞች ለመትከል የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት አስታወቀ።
በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ፕሮግራም በአንድ ጀምበር ከ470 ሺህ በላይ የተለያዩ ለምግብነትና ሁሉ አቀፍ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ገልጿል።
የይርጋጨፌ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ክፍሌ ጅክሶ ላለፉት ስድስት ዓመታት በመላው ሀገሪቱ ተግባራዊ ሲደረግ የቆየው የአረንጓዴ አሻራ ፕሮግራም በርካታ ለውጦችን እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል።
የአረንጓዴ አሻራ የደን ሽፋን ለማስፋትም ሆነ ለማስጠበቅ ፣ ዝናብን በወቅቱ ለማግኘት፣ ለተስተካከለ ስነምህዳር እና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ያለው አስተዋጽዖ ከፍተኛ እንደሆነም ገልጸዋል ።
በይርጋጨፌ ወረዳ የሀገር በቀል ዛፎችንና ለምግብነት የሚውሉ ችግኞችን በብዛት መትከል ላይ ትኩረት መደረጉንና ከነዚህም መካከል የደረሱ ፍራፍሬዎች እንዳሉ ነው የጠቆሙት ።
ዘንድሮም በአንድ ጀምበር ከ470 ሺህ በላይ የተለያዩ ዝሪያ ያላቸውን ችግኞችን በ490 ነጥብ 5 ካሬ መሬት ላይ ለመትከል መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፥ ለዚህም የሚሆኑ ሀገር በቀል ዛፎችን ጨምሮ የፍራፍሬ፣ የቡና፣ የእንሰትና ሌሎችም ችግኞች በበቂ ሁኔታ መዘጋጀታቸውንና በ18ቱም ቀበሌዎች ላይ ለመትከል አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን ተናግረዋል።
ለሀገር አሻራችንን የምናሳርፍበት ቀን በመሆኑ ህብረተሰቡ በነቂስ ወጥቶ በችግኝ ተከላ ፕሮግራም ላይ መሳተፍ አለበት ሲሉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል ።
ዘጋቢ፡ ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የቡርጂ ዞን ምክር ቤት አቶ ትንሳኤ ዮሐንስ ወጌ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አድርጎ ሾመ
የወባ በሽታ ስርጭትን የመከላከልና የመቆጣጠርን ጉዳይ ቀዳሚ ተግባር አድርጎ እየሰራ መሆኑን የስልጤ ዞን ጤና መምሪያ አስታወቀ
አገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ተገልጋዩን ለማርካት እየሰራ መሆኑን የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል አስታወቀ