የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በክልሉ የቤተሰብ ቀንን ለመጀመሪያ ጊዜ በተለያዩ ዝግጅቶች አከበረ

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በክልሉ የቤተሰብ ቀንን ለመጀመሪያ ጊዜ በተለያዩ ዝግጅቶች አከበረ

በዓሉ “የተሻሻለ የቤተሰብ ስራና ገቢ ለሀገር ኢኮኖሚ “በሚል መሪ ቃል በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ተከብሯል።

የክልሉ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ቢሮ ሃላፊና የማህበራዊ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ቤርጉ ፆማ እንደተናገሩት፤ ቤተሰብ በአምራችነት ሚናው የተነቃቃ የስራ ባህል ፈጥሮ ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦው እንዲጠናከር እንዲሁም ትውልድ በመተካት ሂደት ውስጥ ጤናማ እና መልካም ስብዕና ያላቸውን ዜጎች ማፍራት እንዲችል የማድረግ ቀዳሚ ተግባር ነው፡፡

በተለይ ቤተሰብ ደህንነቱ በዘላቂነት እንዲጠበቅ ብሎም ልዩ ልዩ መብቶቹ ተጠቃሚ እንዲሆን ምቹ ሁኔታዎች ሊፈጠሩለት ይገባል ነው ያሉት፡፡

በመሆኑም በዓሉ ሲከበር የቤተሰብ አመራር ክህሎትን በማጠናከር፤ የሥራ ፈጠራ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ የብድር አቅርቦት በማመቻቸት በከተማም ሆነ በገጠር የቤተሰብ የአምራችነት ሚናን ማበረታት ይጠበቃል ብለዋል።

በቢሮው የማህበራዊ ችግር መከላከል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ መሀመድ ሀሰን አንደገለጹት፤ የዘንድሮው የቤተሰብ ቀን በአለም ለ32ኛ ጊዜ እንደ ሀገር ለ3ኛ ጊዜ እንዲሁም በክልሉ ለመጀመሪያ ጊዜ “የተሻሻለ የቤተሰብ ስራና ገቢ ለሀገር ኢኮኖሚ “በሚል መሪ ቃል እየተከበረ ይገኛል።

በዓሉ ሲከበርም ቤተሰብ በተለያዩ የስራ ዘርፎች በመሰማራት የራሱን ዕድገትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥና እንደሀገር ለተያዘው ሁለንተናዊ ብልፅግና መሰረት መሆን ይገባል ብለዋል።

በዓሉ በየደረጃው በሚገኙ በሁሉም ተቋማትና መዋቅሮች እንዲሁም በቤተሰብ ደረጃ ድረስ ይከበራል ተብሏል።

በበዓሉ ላይ የሚዛን ምስጋና አካዳሚ ተማሪዎች የተለያዩ ግጥምና መዝሙሮችን ያቀረቡ ሲሆን ዕለቱን የሚዘክሩ የፓናል ውይይት በማድረግ ተከብሯል።

ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ጣቢያችን