የክልሉን ህዝቦች ሰላም፣ ልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በዘላቂነት ለመፍታት በቅንጅት መስራት እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ: ሰኔ 23/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የክልሉን ህዝቦች ሰላም፣ ልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በዘላቂነት ለመፍታት በቅንጅት መስራት እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊና የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ገለጹ።

“ጠንካራ ክልላዊ አንድነትና አብሮነት ለዘላቂ ሠላምና ብልጽግና” በሚል መሪ ቃል የሠላም፣ የአንድነት የልማት ኮንፈረንስ በወላይታ ሶዶ ከተማ እየተካሄደ ነው ።

በኮንፈረንሱ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ እያደገ የመጣውን የህዝብ ፍላጎት በዘላቂነት መፍታት እንዲያስችል የህዝቡን የሰላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ መመለስና መልካም አስተድደርን ለማጽናት በቅንጅት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል።

በለውጡ መንግስት የተፈጠረውን ሰፊ የፖለቲካ ምህዳር ፣የመልካም አስተዳደርና የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ከተሰሩ ስራዎች መሀከል የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማሳያ መሆኑንም ጠቁመዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህብረብሔራዊነትና ወንድማማችነት ማሳያ መሆኑን ጠቁመው፥ ክልሉ የሰላም የልማት፣ የመቻቻል ተምሳሌት ሆኖ እንዲቀጥል በርካታ ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል።

ክልሉ ከተመሰረተ በኋላ የእድገትና የለውጥ ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀት በግብርና፣ ኢንቨስትመንት፣ ቱሪዝም እና ማዕድን ዘርፍ ተጨባጭ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑን አቶ ገብረመስቀል ተናግረዋል።

በኮንፍረንሱ ሚኒስትሮች፣ ከፌዴራል፣ ክልልና በየደረጃው ከሚገኙ መዋቅሮች የተወጣጡ የክልሉ ተወላጅ ምሁራንና ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የኃይማኖት አባቶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመሳተፍ ላይ ናቸዉ።

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ