የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በወረዳው 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ማድረጉን በኮንታ ዞን አመያ ዙሪያ ወረዳ ግብርና፣ አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ካሣሁን ዳዒሞ ገልጸዋል።
በበልግና በምኸር ወቅቶች ለመትከል ከታቀደው 2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞች በበልግ ተከላ 1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ችግኞች ተተክለው መጠናቀቁን ተከትሎ በምኸር ወቅት ተከላ የተቀረውን 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ለማሳካት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል አቶ ካሣሁን ።
በወረዳው በበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በፍራፍሬ ችግኞች ላይ ትኩረት መደረጉን ያነሱት ኃላፊው በቀጣይም ዘርፈ-ብዙ ጥቅም ባላቸው ችግኞች ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ኃላፊው አብራርተዋል ።
በአመያ ዙሪያ ወረዳ ውስጥ 41 የችግኝ ጣቢያዎች መኖራቸውን በመጠቆም በነዚህ ሁሉም ጣቢያዎች ችግኞቹን ለተከላ ዝግጁ የማድረግ ሥራ ተሰርቷል ብለዋል ።
ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞችም በጥሩ ሁኔታ ላይ መሆናቸውን በመጥቀስ የጽድቀት መጠናቸውም ከ 90 በ መቶ በላይ ስለመሆኑም ነው አቶ ካሣሁን የተናገሩት ።
በወረዳው ከሚገኙ ግብርና ባለሙያዎች መካከልም አቶ ሙሉዓለም ወዳጄ እና አቶ ዘውዴ ሾጋሞ በበኩላቸው ለመርሃ-ግብሩ በችግኝ ጣቢያዎቻቸው ችግኞችንና ጉድጓዶችን ለተከላ ዝግጁ የማድረግ ስራ መጠናቀቁን ገልፀዋል ።
በችግኝ ጣቢያዎች የስራ ዕድሉ ተጠቃሚ የሆኑ ግለሰቦች ከጊዜ ወደ ጊዜ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ስለመሆኑ ተናግረዋል ።
ዘጋቢ ፡ ደረጀ ተፈራ ከዋካ ጣቢያ

More Stories
የወባ በሽታ ስርጭትን የመከላከልና የመቆጣጠርን ጉዳይ ቀዳሚ ተግባር አድርጎ እየሰራ መሆኑን የስልጤ ዞን ጤና መምሪያ አስታወቀ
አገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ተገልጋዩን ለማርካት እየሰራ መሆኑን የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል አስታወቀ
የባስኬቶ ዞን ሕዝብ ምክር ቤት 4ኛ ዙር 10ኛ አመት የሥራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤውን አካሂዷል