የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በወረዳው 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉን በኮንታ ዞን አመያ ዙሪያ ወረዳ ግብርናና አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ገለፀ

የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በወረዳው 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ማድረጉን በኮንታ ዞን አመያ ዙሪያ ወረዳ ግብርና፣ አከባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ካሣሁን ዳዒሞ ገልጸዋል።

‎በበልግና በምኸር ወቅቶች ለመትከል ከታቀደው 2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞች በበልግ ተከላ 1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ችግኞች ተተክለው መጠናቀቁን ተከትሎ በምኸር ወቅት ተከላ የተቀረውን 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ለማሳካት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል አቶ ካሣሁን ።

በወረዳው በበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በፍራፍሬ ችግኞች ላይ ትኩረት መደረጉን ያነሱት ኃላፊው በቀጣይም ዘርፈ-ብዙ ጥቅም ባላቸው ችግኞች ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ኃላፊው አብራርተዋል ።

በአመያ ዙሪያ ወረዳ ውስጥ 41 የችግኝ ጣቢያዎች መኖራቸውን በመጠቆም በነዚህ ሁሉም ጣቢያዎች ችግኞቹን ለተከላ ዝግጁ የማድረግ ሥራ ተሰርቷል ብለዋል ።

ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞችም በጥሩ ሁኔታ ላይ መሆናቸውን በመጥቀስ የጽድቀት መጠናቸውም ከ 90 በ መቶ በላይ ስለመሆኑም ነው አቶ ካሣሁን የተናገሩት ።

በወረዳው ከሚገኙ ግብርና ባለሙያዎች መካከልም አቶ ሙሉዓለም ወዳጄ እና አቶ ዘውዴ ሾጋሞ በበኩላቸው ለመርሃ-ግብሩ በችግኝ ጣቢያዎቻቸው ችግኞችንና ጉድጓዶችን ለተከላ ዝግጁ የማድረግ ስራ መጠናቀቁን ገልፀዋል ።

በችግኝ ጣቢያዎች የስራ ዕድሉ ተጠቃሚ የሆኑ ግለሰቦች ከጊዜ ወደ ጊዜ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ስለመሆኑ ተናግረዋል ።

ዘጋቢ ፡ ደረጀ ተፈራ ከዋካ ጣቢያ