የሴቶችን ሁለንተናዊ ተሣትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሴት አደረጃጀቶችን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ

የሴቶችን ሁለንተናዊ ተሣትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሴት አደረጃጀቶችን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ

በጎፋ ዞን የሴቶች ልማት ህብረት ስትሪንግ ኮሚቴና የሴት ህብረት ሥራ ማህበራት ሪፎርም ዙሪያ ምክክር ተካሂዷል።

የዞኑ ሴቶችና ህጻናት ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ጸጋነሽ እንግዳ፤ ባሳለፍነው አመት የሴቶች ልማት ህብረት ሪፎርም ተደርጎ በዓዲስ መልክ ወደ ስራ መገባቱን ተከትሎ የተመዘገቡ ለውጦች ያሉበትን ደረጃ ለመገምገም ያለመ ውይይት መሆኑን ተናግረዋል።

የሴቶችንና ህፃናትን ጉዳይ አካቶ መተግበር ዙሪያ በሁሉም ባለድርሻ አካላት ያለው አፈጻጸም ወጥነት የሚያንሰው መሆኑን ያነሱት ኃላፊዋ፤ በቀጣይ ተቋማት ልዩ ትኩረት ሊሰጡት እንደሚገባ አሳስበዋል።

የጎፋ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ጋሻለው ገላ፤ ከባለፈው 90 ቀናት እቅድ አኳያ የሴቶች ልማት ህብረት ያሳየው እድገት ከአላማው ረገድ ምን ውጤት አስመዝግቧል የሚለውን መፈተሽ እንደሚገባ ጠቁመዋል።

በህብረት ሥራ ማህበራት ሴቶችን ማሳተፍ ቀጣይነት ያለው ህብረተሰብን ማዕከል ያደረገ አገልግሎት በመሥጠት ሁለንተናዊ ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ለማስመዝገብ ያለው ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን አመላክተዋል።

በኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት አኳያ በጎፋ ዞን ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሴቶችን በልማት ህብረቶች በማደራጀት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ሴቶችና ህጻናት ዘርፍ ኃላፊ ዶ/ር የትነበርሽ አልበኔ አብራርተዋል።

ቁጠባና ብድርን መሠረት ያደረገው የሴቶች ህብረት ስራ ማህበራት ያሉበትን ደረጃ ለመገምገም የመወያያ ሰነድ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጓል።

ዘጋቢ፡ አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን