የሸኮ እና አካባቢዉ ምሁራን ጥናትና ምርምር ማህበር የ2017 በጀት አመት ማጠቃለያ ጉባኤዉን በሸካ ዞን በቴፒ ከተማ በማካሄድ ላይ ነው

የሸኮ እና አካባቢዉ ምሁራን ጥናትና ምርምር ማህበር የ2017 በጀት አመት ማጠቃለያ ጉባኤዉን በሸካ ዞን በቴፒ ከተማ በማካሄድ ላይ ነው

የማህበሩ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ወንዱ ታደሰ በጉባኤው ላይ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፤ የሸኮና አካባቢው ምሁራን ጥናት ምርምር ማህበር በበጀት አመቱ የብሔረሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ መስራቱን ተናግረዋል።

በአካባቢው ሰላምና መረጋጋት እንዲፈጠርና ነዋሪዎች የጠነከረ ማህበራዊ መስተጋብሮች እንዲኖራቸው ልዩነቶችን በሀሳብ የበላይነት መፍታት እንዲቻል የምሁራን ማህበሩ ባለፉት ጊዜያት ከፍተኛ ሚና እንደነበረው ተናግረዋል።

የሸኮና አካባቢው ምሁራን ማህበር የበላይ ጠባቂና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ እንደተናገሩት፤ ማህበሩ ከየትኛውም የፖለቲካ ፓርቲና ድርጅት ነፃ ከመሆኑም ባለፈ አቃፊ በብሄር፣ ቀለምና ማንነት ያልተገደበ በሀሳብ ልዕልና የሚያምን ነው፡፡

ማህበሩ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ባለፉት አመታት በአካባቢው ሰላምና ልማት እንዲረጋገጥ እንዲሁም በህዝቦች መካከል ያለው አብሮነት እንዲጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል፡፡

በጉባኤው ላይ ተገኝተው የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የቴፒ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ወንድሙ ግርማ በበኩላቸው፤ የምሁራን ማህበሩ በብሔሩ ዘንድ የሚታዩ የልማት ችግሮች በቅርበት እንዲፈቱ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በመስራት እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡

በተለይ የሸኮ ብሔር ባህል ታሪክ ወግ እንዲሁም የቋንቋ ልማት ላይ ከሌሎችን ወንድም ህዝቦች ጋር ያለውን አብሮነት በጠበቀ መልኩ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

በጉባኤው ላይ የምሁራን ማህበሩ በበጀቱ ዓመቱ ያከናወናቸውን ስራዎች በሚመለከት በመምህር ኢህአዴግ ገዳ ዝርዝር ሪፖርት ቀርቦ ውይይት እየተደረገ ይገኛል።

በጉባኤው ላይ ከፌደራል፣ ከክልል፣ ከዞንና ከወረዳ የተውጣጡ የተለያዩ አመራሮች እና የሀገር ሽማግሌዎችና የምሁራን ማህበሩ አባላት ተሳታፊዎች ሆነዋል።

ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ጣቢያችን